እስራኤልና ሊባኖስ ከአራት አስርት አመታት ኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ በቀጥታ ተገናኝተው ሊመክሩ ነው። በሀገራቱ መካከል እየተካረረ የመጣውን የጦርነት ፍራቻ ተከትሎ ሁለቱም ሀገራት በሲቪል ተወካዮቻቸው በኩል ውይይት ሊያደርጉ መሆኑን አልጀዚራ ዘግቧል።
የእስራኤል ተወካዮች በደቡባዊ ሊባኖስ ናኩራ ወደ ሚገኙት በአሜሪካ የሚመራ የክትትል ኮሚቴ ጋር ስለመገናኘታቸው ተሰምቷል።
ውይይቱ በእስራኤል ድንበር አቅራቢያ በደቡባዊ ሊባኖስ ናኩራ በሚገኘው የተባበሩት መንግስታት የሰላም አስከባሪ ሀይል ዋና መስሪያ ቤት ነው።
የሊባኖሱ ጠቅላይ ሚኒስትር ናዋፍ ሳላም ከደህንነት ጉዳዮች ባሻገር በሆነው በዚህ ውይይት ላይ ቤሩት ለመሳተፍ እየተዘጋጀች መሆኑን አስታውቀዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ አክለውም ይህ ዘላቂ የሰላም ድርድር አይደለም ነገር ግን ወደ ሰላም የሚደረገውን ጉዞ አንዱ መሰረት ነው ብለዋል።
ይህንን ድርድር የምናደርገው በዋነኝነት የተካረረው ጦርነት ማብቂያ እንዲያገኝ፣ የሊባኖስ ታጋቾች እንዲለቀቁና እስራኤል ከሊባኖስ ግዛቶች ሙሉ ለሙሉ እንድትወጣ ለማድረግ ነው ብለዋል ናዋፍ ሳላም፤
ሊባኖስ የ2002ቱን የአረብ የሰላም እቅድን ትቀበላለች ይኸውም በሁሉም የአረብ ሊግ ሀገራት ስምምነት ላይ የተደረሰና:- የፍልስጤም ነፃ ሀገርነትን የሚያትት፣ በ1967 እስራኤል ከያዘቻቸው ግዛቶች መልቀቅ እንደሚገባት የሚነግር፣ ለፍልስጤም ስደተኞች ፍትሀዊ መፍትሄን መስጠት የሚልና ኋላም ሁሉም አረብ ሀገራት ከእስራኤል ጋር ሰላማዊ ግንኙነት መመስረትን ታላሚ ያደረገ ነው።
እስራኤል በበኩላ ከበፊት እስካሁን ይህንን ስምምነት እንደማትቀበለው ስትናገር ቆይታለች።
እስራኤል አሁንም ቢሆን የሚደረገው ውይይትና ድርድር በሀገራቱ መካከል ኢኮኖሚያዊ ትስስር የሚፈጠርባቸው አስቻይ ሁኔታዎች ላይ ብቻ ነው ሲል ታይምስ ኦፍ እስራኤል ከጠቅላይ ሚኒስትር ቢሮ ባገኘሁት መረጃ ሲል አጋርቷል።
የረቡ ዕለት ስብሰባና የሚደረጉ የድርድር ሀሳቦች ብቅ ያሉት እስራኤልና አሜሪካ ሊባኖስ በሀገሪቷ የሚንቀሳቀሰውን የሄዝቦላህ ታጣቂ ሀይል ትጥቁን ማስፈታት ካልቻለች አይ ዲ ኤፍ መጠነ ሰፊ ዘመቻ ያካሂዳል ማለታቸውን ተከትሎ ነው።
ዘገባው የአልጀዚራና የታይምስ ኦፍ እስራኤል ነው።
NBC Ethiopia
