የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት በየዓመቱ ሐምሌ 29 ቀን የሚያከብረውን የበጎ አድራጎት ቀን በማስመልከት ላለፉት ሶስት ተከታታይ ዓመታት መቄዶንያ በመገኘት ለሦስተኛ ጊዜ በደመቀ ሁኔታ አከበረ።
የመከላከያ ሚኒስቴር የሴቶች እና ማኅበራዊ ጉዳይ ዳይሬክተር ብርጋዴር ጄኔራል ሁሉሀገርሽ ድርስ በስነ-ስርዓቱ ላይ እንደገለጹት፤ ሠራዊቱ የሀገርን ህልውና በጽናት ከመጠበቅ ባሻገር፣ በማዕከሉ ተገኝቶ ፍቅሩን እና ሰብዓዊነቱን በማሳየት ለወገኑ ቀዳሚ ደራሽነቱን አስመስክሯል።
ዳይሬክተሯ አክለውም ሠራዊቱ ከማዕከሉ ጋር ጥብቅ ቤተሰባዊ ቁርኝት እንዳለው ገልጸው፣ ሀገርን በክብር ያገለገሉ አረጋውያንን በመደገፋቸው ኩራት እንደሚሰማቸው ገልፀው ያመጧቸውን ግምታቸው ከ600,000 ሺህ ብር በላይ የሆኑ የተለያዩ የምግብ ፍጆታዎችን፣ ዊልቸር፣ ዋከር፣ አልባሳት፣ የፅዳት ቁሳቁሶች አስረክበው ድጋፉ በቀጣይም ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል።
ለአረጋውያንም ልዩ የምሳ ግብዥ በማድረግ እለቱ ሐምሌ 29ን አረጋውያኑ ልዩ ቀን አድርገው እንዲያስቡት አረጋግጠዋል
የመቄዶንያ መስራችና ዋና ስራ አስኪያጅ የክብር ዶክተር ብንያም በለጠ በበኩላቸው፤ ሠራዊቱ ሕይወቱን አሳልፎ ከመስጠት ባለፈ በማዕከሉ የሚገኙ ወገኖችን በፍቅር እና በርህራሄ በመጎብኘቱ የላቀ ምስጋና አቅርበዋል። በማዕከሉ የሚገኙ የሀገር ባለውለታዎችም ለሠራዊቱ ያላቸውን ፍቅር በምርቃት ገልጸዋል።
በመጨረሻም የቀሩትን የግንባታ ስራዎች በፍጥነት ለማጠናቀቅ ኅብረተሰቡ ድጋፉን አጠናክሮ እንዲቀጥል ጥሪ አቅርበዋል።
