በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የዴሞክራሲ ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል ኃላፊና የብልጽግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ አደም ፋራህ፤ መገናኛ ብዙሃን በነፃነት እንዲሰሩ የሚያስችል ምቹ አውድ ለመፍጠር መንግሥት በርካታ ሥራዎችን ማከናወኑን ገለጹ።
አቶ አደም በፋና ሚዲያ ኮርፖሬሽን ተገኝተው የተቋሙን የሥራ እንቅስቃሴና የማሻሻያ ተግባራት በጎበኙበት ወቅት እንደተናገሩት፤ በተለይም ከለውጡ ወዲህ ሚዲያዎች የለውጡ አካል ሆነው እንዲሻሻሉ ትልቅ ትኩረት ተሰጥቷል።
ኃላፊው አክለውም ቀደም ሲል መገናኛ ብዙሃን በነፃነት እንዳይሰሩ እንቅፋት ሆነው የቆዩ የሕግ ማዕቀፎች እንዲሻሻሉ መደረጉን ጠቁመዋል። ይህም የሚዲያ ተቋማት ያለምንም ገደብ ሙያዊ ኃላፊነታቸውን እንዲወጡ የሚያስችል አዲስ የሥራ ከባቢ መፍጠሩን ገልጸዋል።
ፋና ሚዲያ ኮርፖሬሽንም ይሄንን የተገኘውን የሚዲያ ነፃነት በአግባቡ በመጠቀም በኢትዮጵያ የሚዲያ ታሪክ ውስጥ ጉልህ አሻራ እያሳረፈ እንደሚገኝ አቶ አደም አረጋግጠዋል።
በመጨረሻም ተቋሙ የዘመኑን የመገናኛ ብዙሃን ውድድር ሊቋቋም በሚችል መልኩ ራሱን በዘመናዊ መሣሪያዎችና ምቹ የሥራ አካባቢ መገንባቱን መመልከታቸውን ገልጸዋል።
ፋና ሚዲያ ዘመናዊነትን ከሕዝብ አመኔታ ጋር አቀናጅቶ መጓዙ ተልዕኮውን ይበልጥ እንዲወጣ እንደረዳው ጠቅሰው፤ ተቋሙ አሁን ባለው ጠንካራ ቁመና ተወዳዳሪነቱን ይበልጥ እያላቀ እንደሚሄድ ያላቸውን እምነት ገልጸዋል።
