በኢትዮጵያ ከ2011 ዓመት ጀምሮ መስጠት የተጀመረው የማህፀን በር ጫፍ ካንሰር ክትባት ከዚህ ቀደም ከ14 ዓመት ጀምሮ የሚሰጥ የነበረ ሲሆን አሁን ላይ ከ9 ዓመት ጀምሮ ክትባቱን እንዲጀምሩ እንደሚደርግ ተገልፆል፡፡
ባሳለፉነው 2017 ዓመት ከ9 እስከ 12 ዓመት የእድሜ ክልል ላይ ለሚገኙ በሚሊየን ለሚቆጠሩ ልጃገረዶች በዘመቻ መልክ በየትምህርት ቤቶች የማህፀን በር ካንሰር መከላከያ ክትባት ተሰጥቷል፡፡
በኢትዮጰያ የማህፀን በር ጫፍ ካንሰር ክትባት ከተጀመረ ከ17 ሚሊየን በላይ ልጃገረዶች ክትባቱን ወስደዋል ሲሉ በጤና ሚኒስቴር የእናቶች ፣የህፃናት እና የአፍላ ወጣቶች መሪ ስራ አስፈፃሚ የክትባት አማካሪ ዶክተር አበበ አባዲ ለብስራት ሬዲዮ ተናግረዋል፡፡
በዘመቻ መልክ ብቻ የሚሰጠው ይህ ክትባት በቀጣይ በመደበኛ መልኩ እንዲሰጥ ለማድረግ የተለያዩ ስራዎች እየተሰራ ይገኛል ፡፡ ክትባቱን ለመስጠት ባለሙያዎች በተለያዩ ከተሞች እና ክልሎች ላይ ተገኝተው ለመስጠት ሲሞክሩ በግጭት እና በግንዛቤ እጥረት ምክንያት ክትባቱን ለማከናወን እንደሚቸገሩ ተነግሯል፡፡
ሂዩመን ፓፒሎማ ቫይረስ በግብረ ስጋ ግንኙነት ጊዜ የሚተላለፍ ቫይረስ ሲሆን ለማህጸን በር ካንሰር ዋናው አጋላጭ ነዉ፡፡ ከ99በመቶ በላይ የሚሆነው የማህፀን በር ካንሰር ከዚህ ቫይረስ ጋር በተያያዘ የሚመጣ ነው።የማህጸን በር ካንሰር በኢትዮጵያም ሆነ በዓለም አቀፍ ደረጃ ከጡት ካንሰር ቀጥሎ ሁለተኛዉ ገዳይ በሽታ ነው፡፡
