አዋጅ 1113/2011ን ይተካል የተባለዉ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ማሻሻያ ረቂቅ፤ ለድርጅቶቹ ስራ እክል የሆኑ አሳሪ አንቀፆችን ይዟል የሚል ጥያቄ የተነሳበት ነዉ።
ከጣቢያችን ጋር ቆይታ ያደረጉት የሲቪል ማህበራት ድርጅቶች ምክር ቤት ኘሬዝደንት አቶ አህመድ ሁሴን፤ ምክር ቤቱ አንቀፆቹ እንዲስተካከሉ ከምክረ ሀሳብ ጋር ሲያቀርብ ነበር ብለዋል።
የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ባለሥልጣን እና ፍትህ ሚኒስቴር እያዘጋጁት ያለው ማሻሻያ ረቂቅ አዋጅ ዉስጥ ስጋት የሆኑ አንቀፆች እንዲቀሩ መደረጉንም አንስተዋል።
የአዋጁ ማሻሻያ ረቂቅ አገር በቀል የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ለ’ፖለቲካ አድቮከሲ’፣ የመራጮች ትምህርት፣ ምርጫ መታዘብ እና ማንኛውም ከምርጫ ጋር የተያያዙ ሥራዎችን ለመሥራት ከውጭ የፋይናንስ ምንጭ ገንዘብ እንዳይቀበሉ ይከለክላል።
ሆኖም አሁንም በማሻሻያ ረቂቁ ላይ የሚቀሩ ስራዎች አሉ ያሉት ኘሬዝዳንቱ፤ ይህንንም ለፍትህ ሚኒስቴር ማቅረባቸውን ገልፀዋል።
በቀጣይ ረቂቁ ላይ በሚኖሩ ዉይይቶች ምክር ቤቱ መሻሻል የሚገባቸዉ አንቀፆችን ከነምክረ ሀሳቡ ጋር እያቀረበ ይገኛል ተብሏል።
ምክር ቤቱ እና የሲቪል ድርጅቶቹ በማሻሻያዉ ረቂቅ ላይ ቸልተኛ አልነበሩም ያሉት አቶ አህመድ፤ በተለያዩ ዙሮች ድርጅቶቹ ዉይይቶች ሲያደርጉበት ቆይተዋል ብለዋል።
የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች አዋጅ ማሻሻያ ረቂቅ የ “አፋኝ ህጎችን ስጋት ይፈጥራል” እንዲሁም የሲቪክ ምህዳሩን እንዳያጠበዉ የሚል ጥያቄ የተነሳበት መሆኑ የሚታወስ ነዉ።
