የሲዳማ ተወላጆች በእነዚህ ቀናት ቂም ቁርሾን ሽረው፣ በእርቅ ከአሮጌው ዓመት ወደ አዲስ ዓመት ይሸጋገራሉ።
ለዚህ ተምሳሌትነትም በየደጃፋቸው በእርጥብ እንጨት ባዘጋጁት “ሁሉቃ” በኩል የማለፍ ሥነ ሥርዓት ይፈጽማሉ።
ቤተሰብ በአንድ ላይ በመሰባሰብ በጋራ ማዕድ ይቋደሳል፤ ከአሮጌው ዓመት ወደ አዲስ ዓመት ያሸጋገራቸውን ፈጣሪውንም ያመሰግናል።
በጫምባላላ በዓል የብሔሩ ተወላጆች የባህል ልብሳቸውን ለብሰው ወደ “ጉዱማሌ” አደባባይ በመውጣት፣ በ”ቄጣላ” ባህላዊ ጭፈራ እና በባህላዊ ሥነ ሥርዓቶች በጋራ ያከብራሉ።
በኮሪደር ልማት በአዲስ መልኩ የተሞሸረችው ውቢቷ የሐዋሳ ከተማም ይህን ትዕይንት ለማስተናገድ ተዘጋጅታለች።
ሐዋሳን እንዲጎበኙ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ግብዣ የቀረበላቸው ኢትዮጵያውያንን እና በርካታ የውጭ ሀገራት ቱሪስቶችም በዚህ ትዕይንት ላይ እንደሚታደሙ ይጠበቃል።
ፊቼ ጫምባላላ በተባበሩት መንግሥታት የትምህርት፣ የሳይንስ እና የባህል ተቋም (ዩኔስኮ) በማይዳሰስ የሰው ልጅ ወካይ ቅርስነት ከ10 ዓመት በፊት መመዝገቡ የሚታወስ ነው።
እንኳን ለፊቼ ጫምባላላ በዓል አደረሳችሁ! – “አይዴ ጫምባላላ!”
