የአሜሪካው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ማርኮ ሩቢዮ እና የኢትዮጵያው ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ(ዶ/ር) ባደረጉት የሁለትዮሽ ውይይት በበርካታ ቁልፍ ጉዳዮች ላይ መምከራቸውን የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት አስታውቋል።
ሁለቱ መሪዎች በተለይም በቀጣናዊ መረጋጋት እና በጋራ የደህንነት ጉዳዮች ላይ ትኩረት አድርገው መወያየታቸው ታውቋል።
በውይይታቸው ወቅት ሚኒስትሩ እና ጠቅላይ ሚኒስትሩ በምስራቅ አፍሪካ አስተማማኝ ሰላም እንዲሰፍን ለማድረግ ያላቸውን የጋራ ቁርጠኝነት አረጋግጠዋል።
ከዚህም በተጨማሪ በፀረ-ሽብርተኝነት ተግባራት ዙሪያ ያለውን ትብብር ይበልጥ ማጠናከር በሚቻልባቸው መንገዶች ላይ ሰፊ ምክክር ያደረጉ ሲሆን፣ ይህም በቀጣናው ያለውን የጸጥታ ስጋት ለመቀነስ ከፍተኛ ሚና እንደሚኖረው ተመላክቷል።
የሁለቱን ሀገራት የኢኮኖሚ ብልጽግና ማሳደግ ሌላው የውይይቱ ዋነኛ አካል ነበር። መሪዎቹ የሁለቱን ሀገራት የንግድ እና የኢኮኖሚ ግንኙነት በማጠናከር ረገድ ያላቸውን ፍላጎት የገለጹ ሲሆን፣ በአፍሪካ ቀንድ ለሚታየው ዘላቂ ልማትና የረጅም ጊዜ ደህንነት ጠንካራ መሰረት ለመጣል በጋራ ለመስራት ተስማምተዋል።
