የቅድስት ማሪያም ዩኒቨርስቲ 17ኛውን የዘርፈ ብዙ ጥናት ጉባኤ በበርካታ ወቅታዊ ችግሮች ላይ በማተኮር በዛሬው ዕለት በማካሄድ ላይ ይገኛል።
የዩኒቨርስቲ መስራችና ፕሬዚዳንት ወንድወሰን ታምራት (ዶ/ር)፤ በጉባኤው የቴክኖሎጂ ፈጠራ፣ ዲጂታላይዜሽን፣ የዋጋ ግሽበት፣ የአነስተኛና መካከለኛ ኢንተርፕራይዞችና የፋይናንስ ስርአቶችን የሚደግፉ የህግ ማዕቀፎችን ጨምሮ በርካታ ወቅታዊ ጉዳዮችን የሚያጠቃልል እንደሆነ አስገንዝበዋል።
ጉባኤው ተመራማሪዎችን፣ ባለሙያዎችንና ባለድርሻ አካላትን ተጠቃሚ የሚያደርግ የአካዳሚክ ልውውጥና የሂሳዊ አስተያየቶች የሚቀርቡበት መድረክ መሆኑን ጠቁመዋል።
በተመሳሳይ ሁኔታ ጉባዔው የትምህርትና ማህበራዊ ጉዳዮችን ጨምሮ ዘርፈ ብዙ አቀራረብን በመከተል ከተለያዩ ዘርፎች የተውጣጡ ምሁራን ለችግሮች የመፍትሔ ሀሳብ የሚያበረክቱበት ስለመሆኑ ፕረዚዳንቱ ተናግረዋል።
የጉባኤውን ዘርፍ ብዘሃነት ለማመልከትም ከቅድስት ማሪያም ከዩኒቨርስቲ በተጨማሪ ከአርባምንጭ፣ ወራቤ፣ ባህር ዳር፣ ወልድያ እና መዳ ወላቡ ዩኒቨርሲቲ የተወጣጡ ተመራማሪዎች ፅሁፋቸውን እንደሚያቀርቡ ጠቁመዋል።
ይህ ጥምረትም በዘርፎች መካከል ትብብር በመፍጠር ተፅዕኖ ፈጣሪ የጥናትና ምርምር ተግባራትን ለማከናወን የሚያስችል መሆኑንም ፕሬዝዳንቱ ገልጸዋል።
ለፖሊስ አውጪዎች ግበዓት ሊሆኑ የሚችሉ እሳቤዎች በሰፊው የሚንፀባረቅበት እንደሆነ ወንድወሰን(ዶ/ር) የገለፁ ሲሆን፤ በጉባኤም 12 ጥናታዊ ጽሁፎች ይቀርባሉ ተብሏል።
