የኢትዮጵያ የፈሳሽ ጭነት ማጓጓዣ ባለንብረቶች ማኅበር የአንድ ነዳጅ ጫኝ ቦቴ ጎማ ዋጋ በፊት ከነበረበት ከእጥፍ በላይ በማደጉ ነዳጅን በፍጥነት ወደ መሀል ሐገር የማጓጓዝ ስራው ላይ እንቅፋት እንደፈጠረበት አስታውቋል።
የአንድ የቦቴ ተሽከርካሪ ጎማ ዋጋ 42ሺህ ብር እንደነበር ያስታወሱት የማኅበሩ ፕሬዝዳንት አቶ ጸጋ አሳመረአሁን ዋጋው ከእጥፍ በላይ አድጎ 92ሺህ ብር መድረሱን ተናግረዋል።
ማህበሩ በመግለጫው ዛሬ ሐምሌ 14 ቀን 2018 ዓ.ም. ለመገናኛ ብዙኃን በሰጠው መግለጫ እንዳለው፣ ማኅበሩ በ61 ኩባንያዎች ውስጥ 5 ሺህ 116 ተሽከርካሪዎችን ይዞ አገልግሎት እየሰጠ ይገኛል።
የመለዋወጫ እቃዎች ዋጋ በከፍተኛ ሁኔታ ማሻቀቡን የጠቀሱት የማኅበሩ ሬዝዳንት አቶ ጸጋ፣ መንግስት ለነዳጅ ሻጮች የትርፍ ህዳግ ማሻሻያ ባለማድረጉ እንዲሁም በአንዳንድ ክልሎች በሚያጋጥም የሰላም እጦት እና ዘረፋ ምክንያት የሹፌር አበል እና ተያያዥ ወጪዎችን ሸፍኖ ስራን ማስቀጠል አስቸጋሪ ሆኗል ብለዋል።
የማኅበሩ የቦርድ አባላት ከተለያዩ የመንግስት መስሪያ ቤቶች የተውጣጡ 11 አባላት ያሉት አጥኚ ቡድን በማደራጀት የችግሩን አሳሳቢነት የሚገልጽ የጥናት ሰነድ በማዘጋጀት ለሚመለከታቸው አካላት ማስገባቱንም ማኅበሩ አስታውቋል።
ማኅበሩ መንግስት አሁንም የችግሩን አሳሳቢነት ከግምት ውስጥ በማስገባት የነዳጅ ጫኝ ተሽከርካሪ ቦቴዎች ሙሉ በሙሉ ስራ ከማቋረጣቸው በፊት አስፈላጊውን ሁሉ ድጋፍ እንዲደረግ ጥሪ አቅርበዋል።
