የገቡበት ያልታወቁ ሁለት ጋዜጠኞች “በአስቸኳይ ከስወራ ነጻ እንዲወጡ” የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለሙያዎች ማኅበር ጥሪ አቀረበ።
በአሐዱ ሬዲዮ 94.3 የሚተላለፈው ቅዳሜ ገበያ ፕሮግራም አዘጋጁ ጋዜጠኛ አብዱሰመድ መሐመድ ነሐሴ 5/2017 ዓ.ም በአዲስ አበባ ከተማ ሃያሁለት አካባቢ “ማንነታቸው ባልታወቁ ኃይሎች” ተይዞ መሰወሩን ማህበሩ ገልጿል።
ጋዜጠኛው በድንገት ተይዞ ከተሰወረ ከአራት ቀናት በኋላ ነሐሴ 8/2017 ዓ.ም በጸጥታ ኃይሎች ታጅቦ “ቢሮው መበርበሩን” ተከትሎ፣ ተይዞ የተሰወረው “በመንግሥት የጸጥታ ኃይሎች” መሆኑን መረዳታቸውን ቤተሰቦቹ ለማኅበሩ አስረድተዋል።
በሌላ በኩል በሪፖርተር ጋዜጣ የሚሰራው ጋዜጠኛ ዮናስ አማረ በሚኖርበት ሽገር ከተማ አስተዳደር ኮዬ ፈጬ ኮንደሚኒየም ነሐሴ 7/2017 ዓ.ም ምሽት ላይ “ጭንብል በለበሱ ማንነታቸው ባልታወቁ ኃይሎች” ከቤቱ ተይዞ መወሰዱን ከአካባቢው የጥበቃ አካላት መረዳት መቻሉን ማህበሩ ገልጿል፡፡
ይሁን እንጂ ጋዜጠኛው ከተያዘበት ዕለት ጀምሮ የሚሰራበት የሚዲያ ተቋም ሪፖርተር ጋዜጣም ይሁን ባልደረቦቹ አፈላልገው ማግኘት እንዳልቻሉ ተጠቁሟል።
ጋዜጠኞቹ በወንጀል ተጠርጥረው ቢሆን እንኳን በሕግ አግባብ ተይዘው በ48 ሰዓት ፍርድ ቤት መቅረብ ሲገባቸው፣ ያሉበት አለመታወቁ “አሳሳቢ” መሆኑን ማህበሩ ጠቁሟል።
ጋዜጠኞቹ የተጠረጠሩበት ጉዳይ ካለ የሰብዓዊ መብት ጥሰት ከሚያስከትል ስወራ “ነጻ ወጥተው” “በሕግ አግባብ” ብቻ እንዲዳኙ ማኅበሩ የጠየቀ ሲሆን፤ የገቡበት ያልታወቁ ጋዜጠኞች “በአስቸኳይ ከስወራ ነጻ እንዲወጡ” ጥሪ አቅርቧል።
