የዓለማችን ግዙፍ የመኪና አምራች የሆነው ቶዮታ፤ እንደ ቴስላ እና የቻይናው BYD ያሉ የኤሌክትሪክ መኪና አምራቾች የገበያውን አሰራር በፍጥነት እየቀየሩት መሆኑን አስታውቋል።
ኩባንያው ባለፉት 60 ዓመታት ከ57 ሚሊዮን በላይ በመሸጥ በዓለም ቀዳሚ የሆነችውን «ኮሮላ» መኪና አዲስ ሞዴል ላይ ትልቅ ትኩረት አድርጓል።
የኩባንያው ሊቀመንበር አኪዮ ቶዮዳ፣ በድሮ ስኬት መታበይ አደጋ መሆኑን በመጥቀስ፣ «በዚህ ከቀጠልን ሁሉም ነገር ያበቃል» ሲሉ አስጠንቅቀዋል።
የኩባንያው መሐንዲሶችም የቻይና ኩባንያዎች በቴክኖሎጂ እየቀደሟቸው መሆኑን አምነዋል። አዲሱ የኮሮላ መኪና በነዳጅ፣ በሀይብሪድ እና ለመጀመሪያ ጊዜ ሙሉ በሙሉ በኤሌክትሪክ የሚሰራ አማራጭ ይዞ ይወጣል።
ቶዮታ መኪናው ገበያ ላይ የሚወጣበትን ቀን እስካሁን ይፋ ባያደርግም፣ ይህ አዲሱ የኮሮላ ፕሮጀክት ለኩባንያው የወደፊት ዕጣ ፈንታ እጅግ ወሳኝ ሥራው መሆኑን ገልጿል።
