በአዲስ አበባ ከተማ ለሚገኙ የጤና ባለሙያዎች የትርፍ ሰዓት ክፍያን ጨምሮ አዲስና አጠቃላይ የጥቅማጥቅም ፓኬጅ ከሐምሌ 1 ቀን 2017 ዓ.ም. ጀምሮ ተግባራዊ እንዲሆን ውሳኔ መተላለፉን የከተማ አስተዳደሩ አስታወቀ።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ፐብሊክ ሰርቪስና የሰው ሃብት ልማት ቢሮ እንደገለጸው፣ የከተማዋ ካቢኔ የጤና ባለሙያዎችን ጥቅማጥቅም ለማሻሻል በቀረበለት ጥያቄ ላይ ተወያይቶ አራት አንኳር ውሳኔዎችን ማሳለፉን አስታውሷል።
እነዚህ ውሳኔዎች የጤና ባለሙያዎችን የስራ ሁኔታ ለማሻሻል እና የኑሮ ጫናቸውን ለማቃለል ታስበው የተዘጋጁ መሆናቸው ተጠቁሟል።
ቢሮው በሐምሌ 17 ቀን 2017 ዓ.ም. በጻፈው ሰርኩላር ደብዳቤ ላይ እንደገለጸው፣ ከተፈቀዱት አዳዲስ ጥቅማጥቅሞች መካከል የጤና ባለሙያዎች የትርፍ ሰዓት ክፍያ አፈፃፀማቸው በአገልግሎት ስታንዳርዱ መሰረት እንዲፈፀም የሚለው ይገኝበታል።
በተጨማሪም በዚህ የጥቅማጥቅም ፓኬጅ ደብዳቤ ላይ እንደሰፈረው፣ የጤና ባለሙያዎች የትዳር አጋርና እድሜያቸው ከ18 ዓመት በታች የሆኑ ልጆቻቸው ሙሉ በሙሉ ነጻ የህክምና አገልግሎት እንዲያገኙ ተፈቅዷል። በቀዳማዊ ልጅነት የልማት ፕሮጀክት የተቀጠሩ የቤት ለቤት የምክር አገልግሎት ሰጪዎችም፣ አሰራሩን የጠበቀ ቋሚ የስራ ምድብ እንዲሰጣቸው ውሳኔ ተላልፏል።
ይህ አዲስ ፓኬጅ ከ2018 በጀት ዓመት ( ከሐምሌ 1 ቀን 2017 ዓ.ም.) ጀምሮ ተግባራዊ ሲሆን፣ የጤና ባለሙያዎችን የሞራልና የስራ ተነሳሽነት ከፍ እንደሚያደርግ ይጠበቃል።
CapitalNews
