የኢራኑ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ ሳውዲ አረቢያ ገብተዋል፡፡
ከሳውዲው ልዑል መሐመድ ቢን ሳልማን (ኤም ቢ ኤስ) ጋር በጅዳ ውጤታማ ዲፕሎማሲያዊ ውይይት ማድረጋቸውም ተሰምቷል።
ሰይድ አባስ አራግቺ ከ12 ቀናቱ ጦርነት በኋላ ወደ ሳውዲ አረቢያ ብቅ ሲሉ የመጀመሪያቸው ሆኖ ተመዝግቧል፡፡
ቴህራን እና ሪያድ ዲፕሎማሲያው መንገዶችን እያጠናከሩ መሄዳቸውን የሚጠቁም ጉዞ ተደርጎ ሲወሰድ፣ አገራቱ ቻይና ካሸማገለቻቸው ወዲህ በመካከለኛው ምስራቅ ፖለቲካ ውስጥ ሚናቸውን የጋር እያደረጉት እንደሆነ ያሳያልም ተብሏል።
ስለአሁናዊ የቀጠናው ሁኔታዎች እና ስለተፈጠሩ አዳዲስ ነገሮች የተወያዩ ሲሆን፣ ልዑሉ እና አራግቺ የተሰሩ ስራዎችንም ገምግመዋል።
ውጥረቶችን ለማብረድ የተደረሰው ስምምነት ለሰላም እና መረጋጋት ትልቅ ሚና እንዳለው መሐመድ ቢን ሳልማን ተናግረዋል።
ሳውዱ አረቢያም በመካከለኛው ምስራቅ ሰላማዊ የዲፕሎማሲ መንገዶችን እንደምትከተል ከመወሳቱ ባሻገር፣ የቀጠናው መረጋጋት ለሁለንተናዊ እንቅስቃሴና ዕድገት ቁልፍ ሚና እንደሚኖረውም ታሳቢ ተደርጓል፡፡
