የኢራን ግንኙነት መቋረጥ አቀፍ ደረጃ የተደረገ ረጅሙ የኢንተርኔት መዘጋት ሆኖ መመዝገቡን የኢንተርኔት ክትትል ቡድኑ ኔትብሎክስ አስታወቀ።
የኔትብሎክስ መረጃ እንደሚያመለክተው ኢራን ውስጥ ኢንተርኔት ከተቋረጠ 37ተኛ ቀኑን ይዟል። ባለፉት ከ964 ሰዓት በላይ ለሚሆን ጊዜም ኢራናውያን ከውጭው ዓለም ተቆራርጠዋል።
በኢራን ከውጭ ዓለም ጋር የሚደረግ የኢንተርኔት ግንኙነት በመደበኛው ሁኔታ ሊኖር ከሚገባው አንድ በመቶ ብቻ ሆኖ ቀጥሏል።
ኔትብሎክስ እንደገለጸው፤ በአሁኑ ሰዓት የኢራን የኢንተርኔት መቋረጥ “በየትኛውም አገር ከተመዘገቡት አገር አቀፍ የኢንተርኔት መዘጋቶች ሁሉ እጅግ ረጅሙ” ሆኖ ተመዝግቧል። በኢራን ያለው የኢንተርኔት ሁኔታ “ከዚህ ቀደም ከተመዘገቡ ተመሳሳይ ክስተቶች ሁሉ የከፋ ነው” ብሏል።
ይሁን እንጂ የተወሰኑ ባለሥልጣናት፣ የመንግሥት ደጋፊ የሆኑ ተጠቃሚዎች እና ጋዜጠኞች አሁንም ያልተገደበ የኢንተርኔት አቅርቦት እንዳላቸው ቢቢሲ ተረድቷል። ሌሎች ደግሞ ኢንተርኔት ለማግኘት በርካታ ገንዘብ እየከፈሉ ነው።
የተወሰኑ ሰዎች እንደ ስታርሊንክ ያሉ እና ሌሎች ዘዴዎችን በመጠቀም የሳተላይት ኢንተርኔት ማግኘት ችለዋል። በዚህ መንገድ ኢንተርኔት ማግኘት ግን መዘዙ የከፋ ነው።
ኢራን ውስጥ የኤሎን መስክን ስታርሊንክ መጠቀም ወይም ይዞ መገኘት እስከ ሁለት ዓመት ድረስ ያሳስራል። የአገሪቱ ባለሥልጣናት የሳተላይት ኢንተርኔት የሚጠቀሙ ሰዎች ለማደን ክትትል ያደርጋሉ።
እንደ የኢራን መገናኛ ብዙኃን ዘገባ፤ ጦርነቱ ከተጀመረ አንስቶ “በመቶዎች” የሚቆጠሩ የስታርሊንክ የኢንተርኔት መሣሪያዎች ተይዘዋል።
