በዝምባብዌ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዝዳንት ሉክ ማላባ የተመራ የልዑካን ቡድን በአዲስ አበባ የሥራ ጉብኝት አድርጓል።
ልዑኩ በቆይታው የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት እና የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደርን (ኢንሳ) በመጎብኘት፣ ተቋማቱ ለፍትሕ ሥርዓቱ እያበረከቱት ስላለው የቴክኖሎጂ ድጋፍ ሰፊ ገለጻ ተደርጎለታል።
ፕሬዝዳንት ሉክ ማላባ በጉብኝቱ ወቅት እንደገለጹት፤ የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን በሕግ ዘርፍ ውስጥ መተግበሩ የፍትሕ ሥርዓቱን ውጤታማነትና ቅልጥፍና ለማሳደግ ወሳኝ ሚና አለው።
ቴክኖሎጂን መጠቀም የአሠራር ሂደቶችን ከማቀላጠፉም በላይ፣ ግልጽነትና ተጠያቂነትን ለማረጋገጥ እንደሚረዳ ጠቁመው፤ ከኢትዮጵያ ተሞክሮ ትልቅ ትምህርት ማገኘታቸውን ገልጸዋል።
በተጨማሪም የሁለቱን አገራት የፍትሕ ግንኙነት ይበልጥ ለማጠናከር የሚያስችል የመግባቢያ ስምምነት በፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዝደንት ቴዎድሮስ ምህረት እና በፕሬዝዳንት ሉክ ማላባ መካከል ተፈርሟል።
ይህ ስምምነት በሁለቱ ጠቅላይ ፍርድ ቤቶች መካከል የጋራ ሥራዎችን ለመሥራትና ልምድ ለመለዋወጥ ትልቅ ዕድል እንደሚፈጥር ይጠበቃል።
