በመሃል አዲስ አበባ የቤት ልማትን ጨምሮ ወደ አዳዲስ ተጓዳኝ የግንባታ ስራ ለመሰማራት እቅዱን እያጠናቀቀ የሚገኘው የኢትዮጵያ ባቡር ኮርፖሬሽን ያለበት ከፍተኛ የውጭ እና አገር ውስጥ እዳ ወደ መንግስት እንዲዛወርለት ድርድር እየተደረገ መሆኑ ታወቀ፡፡
ኮርፖሬሽኑ ከባቡር ልማት በተጨማሪ በአገሪቱ የወጪ ገቢ መስመር ከሎጅስቲክ እና ሌሎች ተያያዥ የግንባታ ስራዎች ባሻገር በመሃል አዲስ አበባ ለገሃር አካባቢ ከፍተኛ የቤት ልማት ፕሮጀክት ለማከናወን አቅዷል፡፡
ለአዲሱ የፕሮጀክት እቅድ እንደ የጋራ ልማት፣ እሽሙር/ joint venture እና ሌሎች የተለያዩ አማራጮችን ለመጠቀም ያሰበ መሆኑ ነው የተጠቆመው፡፡
ሆኖም ይህ ግዙፍ እቅድ ከግብ እንዲደርስ አሁን ያለበት ከሩብ ትሪሊየን ብር የሚበልጥ የውጭ እና የአገር ውስጥ እዳ እንዲቃለልለት ስራ እየተሰራ መሆኑ ነው የተገለፀው፡፡
በዚህም የውጭ እዳውን ወደ መንግስት ለማዞር በተለይ ከቻይና ወጪ ገቢ ባንክ ጋር ድርድር እየተደረገ መሆኑን የባቡር ኮርፖሬሽኑ የበላይ የሆነው የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ የኩባንያዎች ምክትል ዋና ስራ አስፈፃሚ የሆኑት አስማ ረዲ ገልጸዋል፡፡
capitalethiopia
