የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ (EIH) እና የማዕድን ሚኒስቴር በሀገሪቱ ያለውን ሰፊ የፖታሽ ማዕድን ሀብት በጋራ ለማልማት የሚያስችል ስምምነት ተፈራረሙ።
ስምምነቱን የሆልዲንግሱ ዋና ስራ አስፈፃሚ ብሩክ ታዬ (ዶ/ር) እና የማዕድን ሚኒስትሩ ሀብታሙ ተገኝ (ኢ/ር) የፈረሙት ሲሆን፣ ዋና ዓላማውም ለዘመናት ሳይለማ የቆየውን የፖታሽ ክምችት ወደ ኢኮኖሚያዊ ጥቅም በመቀየር የሀገሪቱን የኢንዱስትሪ እና የግብርና አቅም ማሳደግ ነው።
ብሩክ ታዬ በወቅቱ እንደገለጹት፣ ይህ ስምምነት ኢትዮጵያ ያላትን የፖታሽ ሀብት ለዓለም አቀፍ ገበያ ለማቅረብና ለማዳበሪያ ምርት ግብዓትነት ለመጠቀም ትልቅ ዕድል ይፈጥራል።
በተለይም ማዕድኑን አጥሮ ከመያዝ ይልቅ በአግባቡ ወደ ስራ የሚያስገቡ ኩባንያዎች ላይ ትኩረት ለሚያደርገው አዲሱ ስትራቴጂ ሆልዲንግሱ ግንባር ቀደም ሚና እንደሚጫወት አረጋግጠዋል።
የማዕድን ሚኒስትሩ በበኩላቸው፣ በአፍሪካ ግዙፍ ከሆነው የሉዓላዊ ሀብት ፈንድ ጋር አብሮ መስራት የማዕድን ዘርፉን ለማሳደግ ስልታዊ ፋይዳ እንዳለው ጠቁመው፣ ሚኒስቴር መስሪያ ቤታቸው ለፕሮጀክቱ ስኬታማነት አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ ገልጸዋል።
ይህ ትብብር የሀገሪቱን የተፈጥሮ ሀብት በኃላፊነት ስሜት በማልማት ለረጅም ጊዜ የኢኮኖሚ እድገት መሰረት ለመጣል ያለመ ነው።
