የኢትዮጵያ መንግሥት ባለሥልጣናት ከተለያዩ የኢትዮጵያ አካባቢዎች ለዶቸ ቬለ የሚዘግቡ ጋዜጠኞች ዘገባ እንዳይሰሩ አገዱ።
ዶቸ ቬለ ከ1980ዎቹ ጀምሮ ኢትዮጵያ ዉስጥ በሚገኙ ዘጋቢዎች አማካይነት የኢትዮጵያን ፖለ,ቲካዊ፣ ምጣኔ ሐብታዊና ማሕበራዊ ጉዳዮችን እና የአፍሪቃ ሕብረትን ጨምሮ ኢትዮጵያ ዉስጥ የሚንቀሳቀሱ አካባቢያዊ፣ አሐጉራዊና ዓለም አቀፍ ድርጅቶች፣ ተቋማትና ማሕበራትን እንቅስቃሴና ክንዋኔዎችን ሲዘግብ ቆይቷል።
ዓለምአቀፉ ማሰራጪያ ጣቢያ ከ 2010 ጀምሮ የወኪሎቹን ቁጥር በማሳደግ መቀሌ፣ ባሕርዳር፣ ደሴ፣ አዲስ አበባ፣ ሐዋሳ፣ ድሬዳዋና አሶሳ በሚገኙ 9 ወኪሎቹ አማካይነት መረጃዎችን በማሰባሰብ ገለልተኛ፣ ሚዛናዊ ዘገባዎችን ለኢትዮጵያ ሕዝብ ያሰራጫል።
ይሁንና የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለሥልጣን ዛሬ በፃፈዉ ደብዳቤዉ ዶቼ ቬለና ወኪሎቹን የኢትዮጵያን ሕግና ደንብ ጥሰዋል፣ ሙያዊ ሥነ-ምግባርን አያከብሩም በማለት ወቅሷል።
ከዛሬ ጀምሮ ኢትዮጵያ የሚገኙ የዶቸ ቬለ ዘጋቢዎችን የሥራ ፈቃድ ለጊዜዉ ማገዱን አስታዉቋል። ባለሥልጣኑ «ጊዚያዊ» ያለዉ እግዳ ሥለሚቆይበት ጊዜ የገለፀዉ ነገር የለም።
