የጤና ሚኒስቴር የስራ ክፍሎች የ2018 እቅዶቻቸውን በማናበብ አዘጋጅተው ማቅረባቸውን የጤና ሚኒስትር ዶ/ር መቅደስ ዳባ የገለጹ ሲሆን፤ የቀረበው እቅድ በአግባቡ ተፈጻሚ እንዲሆን ክትትልና ድጋፍ ማድረግ ያስፈልጋል ብለዋል፡፡
ዶ/ር መቅደስ የ2018 የጤና እቅድ ስኬት በጋራ ኃላፊነት ላይ የተመሰረተ መሆኑን ጠቁመው የጤና ስርዓቱን ለማጠናከርና ጥራት ያለው አገልግሎት አሰጣጥን ለማረጋገጥ ሁሉም የስራ ክፍሎች በቅንጅት ሊሰሩ ይገባል ብለዋል። እንዲሁም ከሚመለከታቸው ተቋማትና ባለድርሻ አካላት ጋር በመተባበር ለተቀናጀ ትግበራም ግልፅ አቅጣጫዎች ሰጥተዋል።
በጤናዉ ዘርፍ የጤና አስተዳደር እና አገልግሎት ሪፎርም በእቅዳቸው አካትተው እንዲተገብሩ የዲጂታላይዜሽን ስራዎችን በማስፋት ወረቀት አልባ አሰራርን መተግበር እና እንደ ጽዱ ጤና ተቋም ያሉ ሃገራዊ ኢንሼቲቭ ፕሮጀክቶችን መተግበር እንደሚያስፈልግ በመድረኩ ተገልጿል።
በመድረኩ የዘርፎች እቅድ ይዘት፣ አላማ፣ ስትራቴጂክ እርምጃዎች እና ዋና ዋና ተግባራት እቅድ ቀርቦ በተሳታፊዎች ውይይት ተደርጎበታል፡፡ መድረኩ መስሪያ ቤቱን ለለቀቁ የቀድሞ አመራሮች እውቅና በመስጠት ተጠናቋል፡፡
