የፍልስጤም ፕሬዚዳንት ማሕሙድ አባስ ሃማስ ትጥቅ እንዲፈታ እና የፍልስጤምን ሕዝብን ለመጠበቅ ዓለም አቀፍ ኃይሎች እንዲሰማሩ ጥሪ አቀረቡ።
አባስ ለፈረንሳዩ ፕሬዚዳንት ኢማኑኤል ማክሮን እና ለሳዑዲ አረቢያው አልጋ ወራሽ መሐመድ ቢን ሳልማን በላኩት ደብዳቤ፤ በጋዛ ያለውን ጦርነት ለማስቆም እና በመካከለኛው ምስራቅ ሰላምን ለማምጣት መወሰድ አለባቸው ብለው የሚያስቧቸውን ዋና ዋና ሃሳቦች አንስተዋል።
በደብዳቤያቸውም “ሃማስ ከዚህ በኋላ ጋዛን አይገዛም፤ የጦር መሳሪያዎቹን እና ወታደራዊ አቅሙን ለፍልስጤም የፀጥታ ኃይሎች ማስረከብ አለበት” ሲሉ ማስፈራቸውን ፍራንስ 24 ዘግቧል።
የአረብ ሀገራትና እና ዓለም አቀፍ ኃይሎች በተባበሩት መንግስታት የፀጥታው ምክር ቤት ተልዕኮ ስር በፍልስጤም እንዲሰማሩ ለመጋበዝ ዝግጁ መሆናቸውንም አባስ አስታውቀዋል።
ፕሬዚዳንቱ በደብዳቤያቸው፤ በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ በዓለም አቀፍ ደረጃ ቁጥጥር የሚደረግበት የፍልስጤም ፕሬዚዳንታዊ እና አጠቃላይ ምርጫን ለማካሄድ ቁርጠኛ መሆናቸውንም ገልጸዋል።
የፍልስጤም መንግስት በግዛቱ ላይ ብቸኛው የፀጥታ አስከባሪ መሆን አለበት ያሉት አባስ፤ ነገር ግን ወታደራዊነት አገዛዝ የሰፈነበት መንግስት የመመስረት ሀሳብ እንደሌላቸው አስታውቀዋል።
ኢማኑኤል ማክሮን በበኩላቸው፤ ፈረንሳይ ለፍልስጤም መንግስት እውቅና ለመስጠት ፍላጎት እንዳላት መናገራቸው የሚታወስ ሲሆን፤ በቅድመ ሁኔታ ግን ሃማስን ትጥቅ መፍታት እንዳለበትና ተጨማሪ ቅድመ ሁኔታዎች መሟላት እንዳለቻው መናገራቸው አይዘነጋም።
