በግጭት ምክንያት ከባድ ጉዳት የተደረሰባቸው የጤና ተቋማት ታደሰው አገልግሎት መስጠት እስኪጀምሩ ለማህበረሰቡ በትምህርት ቤቶችና በድንኳን የጤና አገልግሎት የመስጠት ስራ እየተሰራ ነው ሲል ጤና ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡
በጤና ሚኒስቴር የማህበረሰብ ተሳትፎና የመጀመሪያ ጤና እንክብካቤ መሪ ስራ አስፈፃሚ እስራኤል አታሮ እንደተናገሩት፤ የጤና አገልግሎት የማይቋረጥ ቀጣይነት ያለው ነው፡፡
በሀገሪቱ የሚታዩ ግጭቶች በጤና ተቋማት ላይ ከባድና ቀላል ጉዳት እያደረሱ ነው ብለዋል፡፡
ከግጭት ወጥተው አንፃራዊ ሰላም በሰፈነባቸው አካባቢዎች ቀላል ጉዳት የደረሰባቸው የጤና ተቋማትን በመጠገን አገልግሎት የመስጠት ስራ እየተሰራ ነው ሲሉ ገልጸዋል፡፡
በግጭት ምክንያት ከባድ ጉዳት ደርሶባቸው በቀላሉ ተጠግነው አገልግሎት የማይሰጡ የጤና ተቋማት ባሉባቸው አካባቢዎች ትምህርት ቤቶችን በመጠቀም እና ድንኳን በመዘርጋት አገልግሎት የመስጠት ስራ እየተሰራ ነው ብለዋል፡፡
በድንኳንና በትምህርት ቤቶች የክትባት፤ የቤተሰብ ምጣኔና የተላላፊ በሽታዎች ህክምና እየተሰጠ ነው ሲሉ ተናግረዋል፡፡
ጉዳት የደረሰባቸው የጤና ተቋማት ተጠግነው አገልግሎት እንዲሰጡ ማህበረሰቡንና አጋር አካላትን የማሳተፍ ስራ እየተሰራ ነው ሲሉ ገልጸዋል፡፡
ግጭት ወጥተው አንፃራዊ ሰላም በሰፈነባቸው አካባቢዎች ላይ የሚኖሩ ማህበረሰቦች የጤና አገልግሎት እንዲያገኙ ከጤና ጣቢያ፣ ከጤና ኬላና ከሆስፒታሎች የህክምና ቡድን ተቋቁሟል። ቡድኑ ወደ ስራም ገብቷል ብለዋል፡፡
የዝናብ እጥረት፤ የጎርፍ አደጋ፤ የመሬት መንቀጥቀጥና የተለያዩ ችግሮች የሚከሰቱባቸው ቦታዎችን ታሳቢ ያደረገ አገልግሎት የመስጠት ስራ እየተሰራ ነው ሲሉ ተናግረዋል፡፡
ለማህበረሰቡ ጥራት ያለው የጤና አገልግሎት ተደራሽ ለማድረግ ክልሎች እቅድ አውጥተው እንዲሰሩ የማድረግ ስራ እየተሰራ ነው፤ ተጠናክሮ ይቀጥላል ሲሉ ጠቁመዋል፡፡
ጋዜጣ_ፕላስ
