የትግራይ ክልል መምህራን ውዝፍ ደሞዛቸዉ እንዲከፈላቸው የክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ያስተላለፈውን ውሳኔ፣ የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር አዲስ ደንብ በማውጣት ማገዱ ተገለጸ፡፡
የጊዜያዊ አስተዳደሩ እርምጃ በርካቶችን ያስቆጣ ሲሆን፤ የትግራይ መምህራን ማሕበር ጠበቃ፣ አዲሱን ደንብ በመቃወም ይግባኝ እንደሚሉ አስታዉቀዋል።
የትግራይ መምህራን ማሕበር በጦርነቱ ወቅት ያልተከፈለ የ17 ወራት ደሞዝ ለመምህራን እንዲከፈል በማለት በፌደራሉ መንግስትና በትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር ላይ ክስ መስርቶ ሲከራከር ከቆየ በኋላ፣ ባለፈው ሚያዝያ ወር፣ የትግራይ ጠቅላይ ፍርድ ቤት የአስተማሪዎቹ የ17 ወራት ደሞዝ እንዲከፍል ውሳኔ ማስተላለፉ ይታወሳል።
ፍርድ ቤቱ የፌደራሉ መንግስቱና የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር በአጠቃላይ 5 ነጥብ 4 ቢሊዮን ብር የመምህራን ደሞዝ እንዲከፍሉ ውሳኔ ከሰጠ በኋላ፣ በውሳኔ አፈፃፀም ሂደት ላይ የነበረው የትግራይ መምህራን ማሕበር ክስ፣ ማክሰኞ ሐምሌ 22 2017 ዓ.ም በዋለው ችሎትም፣ በትግራይ ፋይናንስ ቢሮ የባንክ ሂሳብ ታግዶ የነበረው 500 ሚሊዮን ብር ለመምህራኑ እንዲከፈል ተጨማሪ ውሳኔ ሰጥቶ ነበረ።
ይሁንና ሐምሌ 23 ቀን 2017 ዓ.ም ጊዜያዊ አስተዳደሩ ይህን የትግራይ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ውሳኔ የሚሽርና በሕግ ባለሙያዎች ተቃውሞ የቀረበበትን አዲስ ደንብ አውጥቷል።
የትግራይ መምህራን ማሕበር ጠበቃ አቶ ዳዊት ገብረሚካኤል እንደገለጹት፤ አስተዳደሩ እስከ መጨረሻ በፍርድ ቤት ክርክር ላይ ከቆየ በኋላ፥ በሂደቱ ሲሸነፍ ሌላ ደንብ በማውጣት የሕግ ጥሰት ፈጽሟል ብለዋል፡፡
ጊዜያዊ አስተዳደሩ ‘ደንብ’ በማውጣት የፍርድ ቤት ውሳኔ መቀየር እንደማይችል የሚገልፁት አቶ ዳዊት፤ በሀገሪቱ ሕጎች መሰረት ቀጣይ እርምጃዎች እንደሚወሰዱም ተናግረዋል፡፡
DW Amharic
