በሽብር ወንጀል ተጠርጥራ ለሦስት ዓመታት ገደማ በእስር ላይ የምትገኘው ጋዜጠኛ ገነት አስማማው፣ ባጋጠማት የኩላሊት ጠጠር ህመም ምክንያት ተስማሚ ፍራሽ በግል ወጪዋ ለመግዛት እንዲፈቀድላት ለፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት አቤቱታ አቀረበች።
ጋዜጠኛዋ ጥያቄዋን ዕለት መጋቢት 10 ቀን 2018 ዓ.ም ያቀረበችው በጠበቃዋ አቶ ሰለሞን ገዛኸኝ አማካኝነት ለፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት፣ ልደታ ምድብ፣ አንደኛ የህገ መንግስት እና ሕገ መንግስት ላይ የሚፈጸሙ ወንጀሎች ችሎት ነው።
የጤና ሁኔታ እና የማረሚያ ቤቱ ምላሽ
የተከሳሿ ጠበቃ እንደገለጹት፣ ጋዜጠኛ ገነት ላለፉት ሁለት ዓመታት በኩላሊት ህመም ስትሰቃይ የቆየች ሲሆን፣ በቅርቡ በተደረገላት ምርመራ በሁለቱም ኩላሊቶቿ ላይ “ጠጠር” ተገኝቷል። ይህ የጤና እክል ለመቀመጥና ለመተኛት ከፍተኛ ችግር እየፈጠረባት መሆኑን ጠበቃው አስረድተዋል።
በአሁኑ ወቅት በቃሊቲ ማረሚያ ቤት የሚገኘው ፍራሽ “ቶሎ የሚጎደጉድ” በመሆኑ ለህመሟ ምቾት እንዳልሰጣት የገለጹት አቶ ሰለሞን፣ ማረሚያ ቤቱ በሀኪም ትዕዛዝ መሰረት ተስማሚ ፍራሽ እንዲያቀርብ ቢጠየቅም “ከሌሎች ታራሚዎች የተለየ አቅርቦት የለኝም” የሚል ምላሽ መስጠቱን ተናግረዋል።
የፍርድ ቤት ሂደት
ማረሚያ ቤቱ በራሷ ወጪ ፍራሽ ለመግዛት ያቀረበችውን ጥያቄ “ያለ ፍርድ ቤት ትዕዛዝ አልቀበልም” ማለቱን ተከትሎ አቤቱታው ለችሎቱ ቀርቧል። ጋዜጠኛዋ ያቀረበችው ጥያቄ፦
ለኩላሊት ህመም የሚሆን ደረቅ ፍራሽ በግል ገዝታ እንድትጠቀም እንዲፈቀድላት።
ለቃሊቲ ማረሚያ ቤት በዚህ ረገድ ትዕዛዝ እንዲተላለፍላት የሚሉ ናቸው።
ፍርድ ቤቱም የቀረበውን አቤቱታ ተመልክቶ የማረሚያ ቤቱን አስተያየት ለመስማት ለፊታችን ረቡዕ መጋቢት 16 ቀን 2018 ዓ.ም ቀጠሮ ሰጥቷል።
