ዋና ሥራ አስፈጻሚ ፍሬሕይወት ታምሩ መቀመጫውን በእንግሊዝ ለንደን ከተማ ባደረገው አፍሪካ ቢዝነስ መጽሔት የ2026 የአፍሪካ ሴት የቢዝነስ መሪዎች (African Business Women in Leadership 2026) መካከል በመሆን እውቅና ማግኘታቸውን ኩባንያው ገልጿል።
ይህ ዕውቅና በተለይም ባለፉት ዓመታት በሀገራችን በቴሌኮም እና በዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ዘርፍ ዋና ሥራ አስፈጻሚያችን ላስመዘገቡት የላቀ ስኬት እና ላበረከቱት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ትልቅ ተምሳሌት ሆኖ የተሰጠ ዓለም አቀፍ እውቅና ጭምር ነው።
በዋና ሥራ አስፈጻሚዋ በሳል የለውጥ አመራር ብቃት፣ ኩባንያችን ከመደበኛ የቴሌኮም አገልግሎት ባሻገር ወደ ሁለገብ የዲጂታል ተጠቃሚነት እና የኢኮኖሚ እድገት ጉልህ ሚና የሚጫወት ዋና ሞተርነት መሸጋገር ችሏል።
በተጨማሪም የኩባንያው “ቀጣዩ አድማስ፡ ዲጂታልና ከዚያም ባሻገር 2028” ስትራቴጂን በመቅረጽ እና ተግባር ላይ በማዋል፣ ተቋምን በተሳካ ሁኔታ መምራት ብቻ ሳይሆን ለሀገራችን የዲጂታል መጻኢ ዕድል ፅኑ መሠረት በማስቀመጥ ላይ ይገኛሉ፡፡
