የሱዳን ጦር ማዕከላዊ ግዛቶችን ከተቆጣጠረ በወዲህ 1.7 ሚሊዮን ሱዳናውያን ወደ አገራቸው ተመልሰዋል ሲል የተባበሩት መንግስታት አስታውቋል።
ወደ ቀያቸው ከተመለሱት 1.7 ሚሊዮን ሱዳናውያን ውስጥ፤- 1.5 ሚሊዮን የሀገር ውስጥ ተፈናቃዮች ሲሆኑ፤ 200,000 የሚሆኑት ደግሞ ወደ ሌሎች ሀገራት የተሰደዱ ናቸው።
ስደተኞቹ የተመለሱት የሱዳን ጦር ሴናር ፣ ገዚራ እና ካርቱም ግዛቶችን ከተቆጣጠረ ወዲህ መሆኑን ከፓሪስ ሱዳን ትሪቡን ድረ-ገጽ ትናንት ዘግቧል።
“አለም አቀፉ የስደተኞች ድርጅት (አይኦኤም) እና UNHCR ትናንት እንዳስታወቁት ከ1.5 ሚሊዮን በላይ የሚሆኑ የሀገር ውስጥ ተፈናቃዮች ሲሆኑ200,000 የሚጠጉ ስደተኞች ደግሞ ከግብፅ እና ደቡብ ሱዳን ወደ ሀገራቸው ሱዳን ተመልሰዋል” ሲል ድረ-ገጹ ዘግቧል።
በሀገሪቱ ያለው የተፈናቃዮች ቁጥር ጦር ሠራዊቱ ሴናር፣ ገዚራ እና ካርቱም ግዛቶችን ከተቆጣጠረ በኋላ በ13 በመቶ ቀንሷል ተብሏል።
በጎርጎሪያኑ ሚያዚያ 2023 ዓ/ም በፈጥኖ ደራሽ ሀይሉ እና በሱዳን ጦር መካከል የተቀሰቀሰው ግጭት ከ12 ሚሊዮን በላይ ሱዳናውያን ቤት ንብረታቸውን ጥለው እንዲሰደዱ አድርጓል።
ከነዚህ መካከል ዘጠኝ ሚሊዮን የሚሆኑት በሀገር ውስጥ ተፈናቃዮች መሆናቸውን የተባበሩት መንግስታት ድርጅትን ጠቅሶ ዘገባው አመልክቷል።
