በኢትዮጵያ የመጽሐፍ ሕትመት ዋጋ በጣም እየጨመረ በመሄዱ ደራሲያንና አንባቢያን ለከባድ ችግር መዳረጋቸውን ዶቸ ቬለ ዘገበ።
አንጋፋው ደራሲ ኃይለመለኮት መዋዕል እንደገለጹት፤ የወረቀትና የማሳተሚያ ወጪ በመወደዱ ምክንያት ቀድሞ ይካሄድ የነበረው የ20 ሺህ መጻሕፍት ሕትመት ቀርቶ፣ አሁን አብዛኞቹ ወጣት ደራሲያን ከአንድ ሺህ ኮፒ በላይ ማሳትም አልቻሉም።
የሕትመት ዋጋው ቢወደድም የንባብን ባህል ለማሳደግ የሚደረጉ ጥረቶች ግን አልቆሙም።
በቅርቡ በአዲስ አበባ በተካሄደው የንባብ ሳምንትና የመጻሕፍት ዐውደ ርዕይ ላይ ደራስያን፣ አሳታሚዎችና አንባቢያን ተሰባስበው ነበር። በዝግጅቱም ላይ በእስር ቤት ሳሉ በማንበብ ሕይወታቸውን የለወጡ ታራሚዎች ተስፋ ሰጪ ልምዳቸውን ያካፈሉ ሲሆን፤ ንባብ ተስፋ እንዳይቆርጡ እንደረዳቸው ተናግረዋል።
የአንድ ማህበረሰብ የማንበብ ባህል የዕውቀትና የዕድገት መለኪያ ሲሆን፤ የመጻሕፍት መወደድ ግን የሰዎችን የማንበብ ፍላጎት እየጎዳው ነው።
ዘገባው የታዋቂ ደራሲያንን አባባል በመጥቀስ፤ ንባብ አእምሮን ከድንቁርና ነፃ እንደሚያወጣና የመጻሕፍት መወደድ መፍትሔ ካልተበጀለት የትውልዱ ዕውቀት አደጋ ላይ እንደሚወድቅ አሳስቧል።
