ቀጣዩን ሰባተኛው ዙር ሀገር አቀፍ ምርጫ ትግራይ ክልልን ጨምሮ በሁሉም የሀገሪቱ አከባቢዎች ለማካሄድ ዝግጅቶች እየተከናወኑ መሆናቸውን ምርጫ ቦርድ አስታወቀ።
የቦርዱ ሰብሳቢ የሆኑት ሜላተወርቅ ኃይሉ ባሳለፍነው ሳምንት ሀሙስ ሐምሌ 10 ቀን 2017 ዓ.ም ተሻሽሎ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በጸደቀው “የኢትዮጵያ የምርጫ፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች ምዝገባና የምርጫ ሥነ-ምግባር ዐዋጅ” ዙርያ ለመገናኛ ብዙኃን ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል።
ከነባሩ አዋጅ ውስጥ 26ቱ ድንጋጌዎች ላይ ማሻሻያ መደረጉን ያስታወቁት ሰብሳቢዋ፤ አያይዘውም በሰባተኛው ሀገር አቀፍ ምርጫ የቴክኖሎጂ አጠቃቀምን ተግባራዊ ለማድረግ እና የወጣቶች እንዲሁም የሴቶች ተሳትፎን በሚያረጋግጥ መልኩ መሻሻሉን ጠቁመዋል።
ችግሮች ሲፈጠሩም የፓርቲዎች፣ የምርጫ ቦርድ እና የገዢው ፓርቲ አባላት የሚገኙበት የሶስትዮሽ ኮሚቴ ተቋቁሞ በውይይት እንዲፈታ በመደረግ ላይ መሆኑንም አክለዋል።
