ከሰሞኑ መነጋገርያ ሆኖ የሰነበተው የሶስት ጋዜጠኞች በሀይል ታፍነው ከተወሰዱ በኋላ ደብዛቸው መጥፋቱ ነበር። ድርጊቱ በሀገር ውስጥ እንዲሁም በውጭ ያሉ ጋዜጠኞችን እና እንደ ሲፒጄ ያሉ የጋዜጠኞች መብት ተከራካሪ ቡድኖችን ትኩረት ስቦ ቆይቷል።
ታፍነው ተወስደው የነበሩት ጋዜጠኞች አብዱልሰመድ መሐመድ፣ ዮናስ አማረ እና ሐሰን ሰይድ ከእስር ተለቀው በተለያዩ የአዲስ አበባ ስፍራዎች ተበትነው መገኘታቸውን መሰረት ሚዲያ ዘግቧል።
ዛሬ ምሽት 3:00 ገደማ ጋዜጠኞቹ ከአዲስ አበባ ወጣ ባሉ ስፍራዎች ተለቀው መገኘታቸው ታውቋል።
የመጀመርያው ታጋች ነሀሴ 5/2017 ዓ.ም አመሻሽ ላይ ጭምብል ባጠለቁ አካላት ታግቶ የተወሰደው ጋዜጠኛ አብዱልሰመድ መሀመድ ነው።
አብዱልሰመድ አሁን ላይ በሰለንዳ ኤቨንትስ እና ኮሚኒኬሽን እየተዘጋጀ በሚቀርበው ‘ቅዳሜ ገበያ’ ፕሮግራም ላይ ተባባሪ አቅራቢ ነው።
ጋዜጠኛው በቅርቡ ቤተሰቡን የተቀላቀለውን ህፃን ጨምሮ የ4 ልጆች አባት ሲሆን በጋዜጠኝነት ሙያ ወደ 30 ለሚጠጋ አመታት ሰርቷል።
በሌላ በኩል ለበርካታ አመታት በጋዜጠኝነት ሙያ ያገለገለው ጋዜጠኛ ዮናስ አማረ በተመሳሳይ ባሳለፍነው ሳምንት ሀሙስ እለት መኖርያ ቤቱ አቅራቢያ ቀይ ቦኔት በለበሱ የፀጥታ አካላት ታግቶ መወሰዱን የመሠረት ሚድያ ምንጮች ጠቁመው ነበር።
ሪፖርተር ጋዜጣ በባልደረባው እገታ ዙርያ ባወጣው መግለጫ ጋዜጠኛ ዮናስ ከነሐሴ 8 ቀን 2017 ዓ.ም ጀምሮ ሥራ ባለመግባቱ በእጅ ስልኩ ላይ ቢደወልለትም ሆነ ከቤተሰቦቹ ለማጣራት ቢሞከርም ማግኘት አልተቻለም በማለት ባወጣው መግለጫ ጠቁሞ ነበር።
ከሁለቱ ጋዜጠኞች በተጨማሪ ‘Salon Tube’ የተባለ የዩትዩብ ቻናል ባለቤት የሆነው ሀሰን ሰይድ በተመሳሳይ ሀሙስ እለት ተይዞ ተወስዶ ነበር።
ምንጭ:- መሠረት ሚዲያ
