የቡርኪና ፋሶ መንግሥት “ታርጌት ማላሪያ” የተባለው ፕሮጀክት በአገር አቀፍ ደረጃ ወዲያውኑ እንዲቋረጥ ማስታወቁን የተለያዩ የቡርኪና ፋሶ የመገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።
በዘር ምህንድስና የተሻሻሉ ትንኞች የነበሩባቸው ሁሉም መኖሪያዎች ታሽገዋል። የተቀመጡት ናሙናዎችም ባዮሎጂካልና የጤና ደህንነትን በሚያረጋግጥ ጥብቅ መመሪያ መሰረት እንደሚወድሙ ተገልጿል።
የቡርኪና ፋሶ ባለሥልጣናት ይህን ውሳኔ ያጸደቁት የሕዝብ ጤናን፣ አካባቢን እና የሀገሪቱን ሳይንሳዊ ሉዓላዊነት ለመጠበቅ አስፈላጊ በመሆኑ ነው ብለዋል።
ይህ እርምጃ ቡርኪና ፋሶ የዘር ምህንድስናን የሚያካትቱ የሳይንስ ፕሮጀክቶችን የምትቆጣጠርበት መንገድ ላይ ትልቅ ለውጥ የሚያመጣ መሆኑን ያሳያል ሲሉም ተናግረዋል።
በአሜሪካዊው ቢሊየነር ቢል ጌትስ የገንዘብ ድጋፍ የሚደረግለት “ታርጌት ማላሪያ” ፕሮጀክት ትንኝን በዘር ምህንድስና በመቀየር የወባ በሽታን ስርጭት ለመቀነስ ያለመ ነበር።
