የቴስላ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ኢሎን መስክ፣ በሚቀጥሉት አስር ዓመታት እቅዶቹን ከግብ ካደረሰ፣ የአንድ ትሪሊዮን ዶላር የጉርሻ ማዕቀፍ እንደሚሸልም የኩባንያው ቦርድ አስታውቋል።
የዓለማችን ባለሀብት የሆነው መስክ ሽልማቱን ለማግኘት የቴስላን የኩባንያ ዋጋ በስምንት እጥፍ ማሳደግ፣ አንድ ሚሊዮን የአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ሮቦቶችን መሸጥ፣ ተጨማሪ 12 ሚሊዮን የቴስላ ተሽከርካሪዎችን መሸጥ እንዲሁም ሌሎችንም ከባድ ግቦች ማሳካት እንዳለበት ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
መስክ በቀጥታ ደሞዝ አሊያም ጉርሻ የማያገኝ ሲሆን፤ ይልቁንም ግቡን ካሳካ ቀስ በቀስ አንድ ትሪሊዮን ዶላር የሚያወጡ ድርሻዎችን እንደሚሸለም ተነግሯል።
የኩባንያው ቦርድ ነዋይ አፍሳሾች ይህን የሽልማት ማዕቀፍ ደግፈው ድምፅ እንዲሰጡ ጥሪ አቅርቧል።
የቦርዱ ሰብሳቢ ሮበን ዴንሆልም፤ “ዛሬ የማይታሰብ የሚመስል እድገት በአዲስ ሀሳብ፣ በተሻለ ቴክኖሎጂና በግሩም ፈጠራ እውን ይሆናል” ብለዋል።
“በቀላል አነጋገር ኢሎንን ማበረታታት ቴስላ እነዚህን ግቦች ለማሳካትና በታሪክ ትልቅ ዋጋ ያለው ኩባንያ ለመሆን መሰረታዊ ነው” ሲሉም አክለዋል።
ሰብሳቢዋ አክለውም፤ ለኢሎን መስክ የሚሸለመው ድርሻ “ለባለራዕዩ መሪያችን አፈፃፀሙን ጫፍ ላይ ያደርሳል” ብለዋል።
ይህ ዜና የተሰማው መስክ ቃል ተገብቶለት የነበረው 50 ቢሊዮን ዶላር ሽልማት በፍርድ ቤት ለባለድርሻዎች ፍትኃዊ አይደለም በሚል ውድቅ ከተደረገበትና 29 ቢሊዮን ዶላር የሚያወጣ ድርሻ በተሸለመ ማግስት ነው።
