ኢትዮጵያ በጊዜው ያልከፈለችውን የአንድ ቢሊዮን ዶላር ዩሮ ቦንድ በተመለከተ በገንዘብ ሚኒስቴር እና በግል አበዳሪዎች ኮሚቴ መካከል ሲደርግ የነበረው ድርድር ያለ ስምምነት ተጠናቀቀ።
ገንዘብ ሚኒስቴር ለቀናት በቆየው ንግግር “ጉልህ መሻሻል” መታየቱን ቢገልጽም የአበዳሪዎች ኮሚቴ ግን ድርድሩ “ፍሬ አልባ” ደረጃ ላይ በመድረሱ “ሕጋዊ አማራጭ” ሊከተል እንደሚችል አስታውቋል።
ገንዘብ ሚኒስቴር፤ የብድሩን አከፋፈል ሁኔታ ለማስተካከል ሲካሄድ የቆየው ድርድር ያለ ስምምነት መጠናቀቁን ያስታወቀው ትናንት ማክሰኞ ጥቅምት 4/2018 ዓ. ም. ባወጣው መግለጫ ነው።
በፈረንሳይ ፓሪስ ከተማ የተካሄደው ድርድር ላይ የኢትዮጵያ ልዑክ ‘ዋይት ኤንድ ኬዝ’ የተሰኘውን የሕግ አማካሪ እና ‘ላዛርድ’ የተባለውን የፋይናንስ አማካሪ ይዞ ቀርቧል።
የቦንዱ ገዢዎችን የወከለው የአበዳሪዎች ኮሚቴም በተመሳሳይ ድርድሩ ላይ የተገኘው ከሕግ እና የፋይናንስ አማካሪዎቹ ጋር ነው።
ኢትዮጵያ በድርድሩ ወቅት፤ ሁሉንም አበዳሪዎችን በእኩልነት ለማስተናገድ በያዘችውን መርሕ ጸንታ እንደቀጠለች በገንዘብ ሚኒስቴር መግለጫ ላይ ሰፍሯል።
ኮሚቴው በአሁኑ ሰዓት ድርድሩ “ፍሬ አልባ” ደረጃ ላይ ነው የሚል ድምዳሜ ላይ መድረሱንም ተናግሯል። “የሕግ እርምጃን ጨምሮ ሁሉንም አማራጮች እያጤነ” መሆኑን እንዳስታወቀም ሮይተርስ ዘግቧል።
