የግል ድርጅቶች ሠራተኞች ማኅበራዊ ዋስትና አስተዳደር የጡረታ ፈንድ ኢንቨስትመንቱን ለማሳደግና አማራጮቹን ለማስፋት ወደ አዲሱ የኢትዮጵያ ሰነደ ሙዓለ ንዋይ ገበያ ለመግባት ዝግጅት እያደረገ መሆኑን ለፓርላማ አስታወቀ።
የአስተዳደሩ ዋና ዳይሬክተር አቶ አባተ ምትኩ እንደገለጹት፣ ተቋሙ ከሦስት ዓመት በፊት በተደረገ የአዋጅ ማሻሻያ መሠረት ከግምጃ ቤት ሰነድና ከመንግሥት ቦንድ ውጭ በሌሎች ዘርፎች ላይ ኢንቨስት ለማድረግ ቢፈቀድለትም፣ በአዲስ አበባ የታቀደው የሪል ስቴት ኢንቨስትመንት በመሬት አቅርቦት እጥረት ምክንያት በመጓተቱ ትኩረቱን ወደ ካፒታል ገበያው አዙሯል።
አስተዳደሩ ባለፈው በጀት ዓመት 183 ቢሊዮን ብር ኢንቨስት በማድረግ 14 ቢሊዮን ብር ትርፍ ያስመዘገበ ሲሆን፣ ባለፉት ስድስት ወራት ደግሞ 25.8 ቢሊዮን ብር ገቢና 10.8 ቢሊዮን ብር ትርፍ ማግኘቱን ጠቁሟል።
ሆኖም በአማራና በኦሮሚያ ክልሎች ባለው የጸጥታ ችግር ምክንያት የታቀደውን ያህል የጡረታ መዋጮ መሰብሰብና ውዝፍ ክፍያዎችን ማስመለስ ፈታኝ እንደሆነበት የተገለጸ ሲሆን፣ በያዝነው በጀት ዓመት 55 ቢሊዮን ብር መዋጮ ለመሰብሰብና 20 ቢሊዮን ብር የኢንቨስትመንት ትርፍ ለማግኘት አቅዶ እየሠራ ይገኛል።@SECO
