አፍሪካን ከፖሊዮ፣ ከኮሌራ እና ከሌሎች በውሃ ወለድ ከሚመጡ በሽታዎች ሙሉ በሙሉ ለመታደግ የክትባት ዘመቻዎች የውሃ፣ የንፅህና አጠባበቅ እና የግል ንፅህና መሰረተ ልማቶች ጋር ተቀናጅተው ሊመሩ እንደሚገባ የዘርፉ መሪዎች አሳሰቡ።
ይህ ጥሪ የቀረበው በ39ኛው የአፍሪካ ህብረት ጉባኤ ጎን ለጎን፣ የዓለም ጤና ድርጅት የአፍሪካ ቀጠናዊ ቢሮ እና የአፍሪካ ህብረት የጤና ኮሚሽን ከናይጄሪያ እና ዛምቢያ መንግስታት ጋር በመተባበር ባዘጋጁት ከፍተኛ የጎንዮሽ መድረክ ላይ ነው።
በመድረኩ ላይ ንግግር ያደረጉት የዓለም ጤና ድርጅት የምስራቅ ሜዲቴራኒያን ቀጠናዊ ዳይሬክተር ዶ/ር ሀናን ባልኺ በበኩላቸው፣ በአግባቡ የማይወገዱ ፍሳሾች እና የንጹህ ውሃ እጥረት ለፖሊዮ እና ለኮሌራ ተህዋሲያን መራባት ዋነኛ መንገዶች መሆናቸውን ገልጸዋል።
እንደ ዳይሬክተሯ ገለጻ፣ የውሃ እና የንጽህና አገልግሎቶችን በማስፋፋት ብቻ በዓለም አቀፍ ደረጃ በየዓመቱ የሚከሰተውን የ1.4 ሚሊዮን ሰዎችን ሞት መታደግ ይቻላል።
የኢትዮጵያ ፖሊዮ ፕላስ ኮሚቴ ሰብሳቢ ትዕግስት ይልማ በበኩላቸው ክትባቶች ህይወትን እንደሚያድኑ ገልጸው፣ ነገር ግን ዘላቂ ውጤት ለማምጣት ንጹህ ውሃ እና የተሟላ የሳኒቴሽን አገልግሎት የግድ አስፈላጊ መሆናቸውን አጽንኦት ሰጥተዋል። በሽታው የሚከሰትበትን ስር ነቀል መንስኤ ካልፈታን ክትባት ብቻውን ዋስትና ሊሆን አይችልም” ሲሉም መንግስታት ለዘርፉ ቅድሚያ እንዲሰጡ ጠይቀዋል።
በመሆኑም የአፍሪካ ሀገራት ፖሊዮን ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ለማጥፋት በሚያደርጉት ጥረት ውስጥ በትምህርት ቤቶች እና በጤና ተቋማት የውሃ እና የአካባቢ ጤና አጠባበቅ አገልግሎትን ማጠናከር፤ በግጭት ቀጠናዎች የሚገኙ የውሃ እና የጤና መሰረተ ልማቶችን ከጥቃት መከላከል እንደሚገባቸው በመድረኩ ላይ ተመላክቷል።
በአሁኑ ወቅት 31% የሚሆነው የአፍሪካ ህዝብ ብቻ ደህንነቱ የተጠበቀ የሳኒቴሽን አገልግሎት የሚያገኝ ሲሆን፣ መሰረታዊ የንጽህና አገልግሎት ተደራሽነቱም 28% ብቻ መሆኑ ተገልጿል። ይህም በውሃ ወለድ የሚመጡ በሽታዎችን ለመከላከል የሚደረገውን ጥረት አሁንም ትልቅ ተግዳሮት አድርጎታል።
ይሁን እንጂ ሮተሪ እና የዓለም ጤና ድርጅት አፍሪካን ከፖሊዮ ነፃ የማድረጉን ጉዞ ዳር ለማድረስ ከመንግስታት እና ከማህበረሰቡ ጋር በጋራ እንደሚሰሩ ዳግም አረጋግጠዋል።
