በሱዳን የሚገኘው የተመድ የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽን ይፋ ባደረገው መረጃ መሰረት፣ በሱዳን ብሉ ናይል ግዛት ውስጥ ብቻ ከ12,000 በላይ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች ይገኛሉ።
በአሁኑ ወቅት በሱዳን ውስጥ በአጠቃላይ 68,750 ኢትዮጵያውያን ስደተኞችና ጥገኝነት ጠያቂዎች እንደሚገኙ የተገለጸ ሲሆን፣ አብዛኞቹ (65 በመቶው) በገዳሪፍ ግዛት ውስጥ ይኖራሉ።
ይህ አሃዝ የወጣው በሱዳን ያለው የእርስ በርስ ግጭት በበረታበትና በድንበር አካባቢ የጸጥታ ስጋቶችና የፖለቲካ ውጥረቶች እየጨመሩ በመጡበት ወቅት ነው።
በሱዳን እየተካሄደ ያለው ጦርነት የስደተኞችን ሕይወት እጅግ አስቸጋሪ እያደረገው ሲሆን፣ በሺዎች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን በተለይም የትግራይ ተወላጆች ለከፍተኛ የምግብና የመድኃኒት እጥረት መጋለጣቸው ተነግሯል።
በጦርነቱ ምክንያት ረድኤት ሰራተኞች ከአካባቢው መውጣታቸውና የረድኤት አቅርቦት መቋረጡ ስደተኞቹን ለከፋ አደጋ አጋልጧቸዋል። በዚህም ምክንያት ብዙዎቹ ስደተኞች በሕይወታቸው ላይ ከፍተኛ ስጋት እንደተጋረጠባቸው በመግለጽ፣ ዓለም አቀፍ ጣልቃ ገብነት እንዲደረግና ወደ ሀገራቸው እንዲመለሱ በተደጋጋሚ ድምጻቸውን እያሰሙ ይገኛሉ።
