ፌስቡክን የሚያስተዳድረው ሜታ ኩባንያ፣ የድርጅቱ መስራች ማርክ ዙከርበርግን በትክክል የሚመስል “የAI ክሎን” (ሰው ሰራሽ ቅጂ) እየሰራ መሆኑ ተሰምቷል።
ይህ AI የዙከርበርግን የአነጋገር ዘይቤ፣ ድምፅና የአስተሳሰብ መንገድ እንዲቀዳ ተደርጎ የሚሰለጥን ሲሆን፣ ዋና ዓላማውም ሰራተኞች ከዋናው ስራ አስኪያጅ ጋር በቀጥታ እያወሩ እንዳሉ እንዲሰማቸው ለማድረግ ነው። ዙከርበርግ ራሱ ይህ AI የኩባንያውን የወደፊት ዕቅዶች በሚገባ እንዲያውቅ ለማድረግ ስልጠናው ላይ በሳምንት እስከ 10 ሰዓት እየተሳተፈ ይገኛል።
አዲሱ ቴክኖሎጂ ሰራተኞች ከAIው ጋር በገሃዱ ዓለም እንደሚደረግ ውይይት እንዲነጋገሩ ያስችላቸዋል ተብሏል። ሜታ ቀደም ሲል እንደ ስኑፕ ዶግ እና ኬንዳል ጄነር ያሉ ታዋቂ ሰዎችን የሚመስሉ የቻትቦት ቴክኖሎጂዎችን ሰርቶ የነበረ ቢሆንም፣ ብዙም ሳይሳካለት ቀርቶ በ2024 ዘግቷቸው ነበር።
አሁን ግን ኩባንያው ትኩረቱን ወደ ራሱ መስራች በማዞር፣ ሰራተኞች ከዙከርበርግ ጋር ያላቸውን ግንኙነት ይበልጥ ለማቀራረብ በ”ሱፐር ኢንተለጀንስ ላብስ” በኩል ስራውን ጀምሯል።
ከዚህ በተጨማሪ ዙከርበርግ ለራሱ ብቻ የሚያገለግል “CEO Agent” የተባለ ሌላ የAI ረዳት እያስገነባ ነው። ይህ ረዳት በኩባንያው ውስጥ ያሉ መረጃዎችን በፍጥነት እንዲያገኝ የሚረዳው ሲሆን፣ ዙከርበርግ አሁን ላይ በራሱ ኮዲንግ እስከመስራት ድረስ በቴክኖሎጂ ስራው ላይ ጠንክሮ እየተሳተፈ መሆኑ ተገልጿል።
ሜታ የሜታቨርስ (Metaverse) ህልሙን በመቀነስ፣ አሁን ላይ ሙሉ አቅሙን ወደ ሰው ሰራሽ አስተውሎት (AI) በማዞር ላይ ይገኛል።
