የኢትዮጵያ አየር መንገድ፣ የበረራ መዳረሻዎቹን ይበልጥ ለማስፋትና በአህጉሪቱ ያለውን ተደራሽነት ለመጨመር እስከ 50 የሚደርሱ አዳዲስ የመንገደኞችና የጭነት አውሮፕላኖችን ለመግዛት የመጨረሻ ውሳኔ ላይ መድረሱን ብሉምበርግ ዘግቧል።
የአየር መንገድ ግሩፑ የንግድ ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ ለማ ያዴቻ እንደገለጹት፣ በአሁኑ ወቅት የትኞቹን አውሮፕላኖች መግዛት እንዳለባቸው የሚወስን የመጨረሻ የቴክኒክና የፋይናንስ ግምገማ እየተደረገ ይገኛል።
አየር መንገዱ 25 መካከለኛ መጠን ያላቸው የመንገደኞች አውሮፕላኖችን በቀጥታ ለመግዛት ያቀደ ሲሆን፣ ተጨማሪ 10 አውሮፕላኖችን ደግሞ ወደፊት በተመሳሳይ ዋጋ የመግዛት መብት የሚያካትት ስምምነት ያደርጋል።
ከዚህ በተጨማሪም እስከ 16 የሚደርሱ የጭነት አውሮፕላኖችን ለመግዛት ውሳኔ ላይ መቃረቡ ታውቋል።
ለዚህ ግዙፍ ግዢ የአሜሪካው ቦይንግ፣ የፈረንሳዩ ኤርባስ እና የብራዚሉ ኤምብራየር ኩባንያዎች እርስ በርስ እየተፎካከሩ ይገኛሉ።
አየር መንገዱ የመጨረሻውን ውሳኔ በሚቀጥሉት ጥቂት ሳምንታት ውስጥ ይፋ ያደርጋል ተብሎ የሚጠበቅ ሲሆን፣ ይህም ምናልባትም በሚቀጥለው ሳምንት ከሚጀምረው የዓለም አቀፍ ትዕይንት/ Farnborough Air Show ጋር ተያይዞ ሊገለጽ እንደሚችል ተገምቷል።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ በአሁኑ ወቅት ከ170 በላይ ዘመናዊ አውሮፕላኖችን እያበረረ የሚገኝ ሲሆን፣ አዳዲሶቹ አውሮፕላኖች የአየር መንገዱን የበረራ መርከቦች ዕድሜ በአማካይ ከስምንት ዓመት በታች አድርጎ ለመጠበቅና በአምራቾች ዘንድ ያለውን የተፈላጊነት ዕድል ቀድሞ ለመጠቀም ትልቅ እገዛ ያደርጋሉ።
