አዲሱ የክለቡ ፕሬዝዳንት እስራኤል ደገፋ (ዶ/ር) ክለብ አሰልጣኝ ገብረ መድህን ኃይሌን ባስፈረመበት ይፋዊ መግለጫ ላይ የተለያዩ ጉዳዮችን አንስተዋል።
ኢትዮጵያ ቡና በዘላቂነት ላይ ትኩረቱን አድርጎ እንደሚሰራ የጠቆሙት ፕሬዝዳንቱ “ተረጂ ሳይሆን ረጂ” መሆን እንዲችሉ እየሰሩ እንደሚገኙ ጠቁመዋል።
“ቤቴን ለመረከብ የቤት ስራዬን ስሰራ ቆይቻለው።” ያሉት ዶ/ር እስራኤል ከሚድያ ጋር ያልተገናኙትም በዚሁ ምክንያት መሆኑን ጠቁመዋል።
“የስቴድየም የዲዛየን ስራ ጨርሰናል። 8 ቢልየን ይፈጃል። በቀጣይ እሱን የማስጀመር ስራውን እንሰራለን።” ሲሉም ክለቡ የስታድየም ባለቤት ለመሆን ያለውን እቅድ ገልፀዋል።
“ኢትዮጵያ ቡና እንደምትሉት ደሃ አይደለም።” ያሉት ፕሬዝዳንቱ “ከሌሎች ክለቦች የተሻለ ሃብትም ፣ መገልገያም አለን።” ሲሉ ገልፀዋል።
ከአሰልጣኝ ገብረ መድህን ኃይሌ ጋር ያሰሩት ውል የ2 አመታት የመሆኑ ምክንየትም ከፋይናንስ ጋር እንደማይያያዝ አሳውቀዋል።
ከደሞዝ እና ጥቅማ ጥቅም ጉዳዮች ጋር በተያያዘ በማህበራዊ ሚዲያ የሚናፈሰው ከእውነት የራቀ መሆኑ ሲጠቆም ፣ የገንዘቡ መጠን ምን ያህል ነው የሚለው ጉዳይ በሁለት ተዋዋይ ወገኖች መሃል ስምምነት ሳይኖር ምላሽ እንደማይሰጥበት ተገልጿል።
