በትግራይ ክልል የሚንቀሳቀሰው ተቃዋሚ ፓርቲ ሳልሳይ ወያነ ትግራይ “የአስፈላጊ የሰብአዊ እርዳታ አቅርቦቶች እጥረት” ምክንያት በክልሉ በሚገኙ የተፈናቃዮች መጠለያ ካምፖች ውስጥ “የሚሞቱ ሰዎች ቁጥር በፍጥነት እየጨመረ ነው” ሲል አስታወቀ።
በመጠለያ ካምፖቹ ያለው የሰብዓዊ ቀውስ እጅግ እየከፋ መጥቷል ሲል ገልጿል።
ፓርቲው ትላንት ግንቦት 4 ቀን 2017 ዓ.ም ባወጣው መግለጫ “በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ተፈናቃዮች እና ስደተኞች” “በአስከፊ ችግር ውስጥ እየኖሩ ነው” ሲል አስታውቋል፤ “በግልጽ የሚታይ የፖለቲካ ፍላጎት ማጣት እና እንደገና ግጭት ሊያገረሽ ይችላል የሚለው ፍራች” ሳቢያ ተፈናቃዮችን ለመታደግ “የአጭር እና የረጅም ጊዜ እፎይታ የማግኘት እድሉ በፍጥነት እየጠፋ ነው” ሲል አስጠንቅቋል።
ለሁኔታው መባባስ የፕሪቶሪያ የሰላም ስምምነት ሙሉ በሙሉ አለመፈጸም እና በኢትዮጵያ እና ኤርትራ መካከል የተፈጠረው ውጥረት አስተዋጽኦ ማድረጉን ጠቁሟል።
በቀጠናው እየተስተዋሉ ያሉ እድገቶች “እጅግ ገዳይ የሆነ ግጭት እንደገና ሊቀሰቅሱ ይችላል” ሲል አስጠንቅቋል።
ሳልሳይ ወያነ ትግራይ ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ “እነዚህን እየተባባሱ ያሉ የሰብአዊ እና የደህንነት ችግሮችን ለመፍታት በጉዳዮቹ አሳሳቢነት ልክ ጥረት እንዲያደርግ ጠይቋል።
የኢትዮጵያ መንግስት እና የሚመለከታቸው የቀጠናው አካላት “ጊዜው ከመርፈዱ በፊት ልዩነቶቻቸውን በሰላማዊ መንገድ ለመፍታት እንዲሰሩ” ሲል አሳስቧል።
አለም አቀፉ ማህበረሰብን “ጆሮ ዳባ ልበስ ብሎ ዝምታን መርጧል” ሲል የተቸው ፓርቲው ይህም “ተቀባይነት የሌለው እና በጣም አሳሳቢ” ነው ሲል ኮንኗል።
አዲስ እስታንደርድ