ዝነኛው ደራሲና ገጣሚ በዕውቀቱ ሥዩም በስፔን ባርሴሎና በሚካሄደው 41ኛው ዓለም አቀፍ የግጥም ፌስቲቫል ላይ ግጥሞቹን እንዲያቀርብ ተጋብዟል።
ይህ ታላቅ ፌስቲቫል ከግንቦት 6 እስከ 13 ቀን 2018 ዓ.ም. የሚቆይ ሲሆን፣ በዕውቀቱ ግንቦት 13 ቀን በታሪካዊውና እጅግ ውብ በሆነው ‘ፓላው ዴ ላ ሙዚካ ካታላና’ አዳራሽ በሚካሄደው የመዝጊያ ሥነ-ሥርዓት ላይ ግጥሞቹን ለዓለም ያሰማል።
ገጣሚው በዚህ መድረክ ከተለያዩ አህጉራት ከተመረጡ 7 ታዋቂ ገጣሚዎች ጋር በመሆን የኢትዮጵያን ሥነ-ጽሑፋዊ ለዛ በዓለም መድረክ ላይ ያስመሰክራል።
የባርሴሎና ዓለም አቀፍ የግጥም ፌስቲቫል እ.ኤ.አ ከ1985 ጀምሮ በየዓመቱ የሚካሄድና በዓለም ላይ ካሉ ጥንታዊና ዝነኛ የግጥም መድረኮች አንዱ ነው።
ፌስቲቫሉ በካታሎኒያ ባህል ውስጥ ትልቅ ቦታ ያለው ሲሆን፣ ግጥም ከሙዚቃ፣ ከዕይታ ጥበብና ከቪዲዮ ጋር ተቀናጅቶ የሚቀርብበት ልዩ ጥበባዊ ድግስ ነው።
በዕውቀቱ ሥዩም የግጥም ስራዎቹን የሚያቀርብበት ‘ፓላው ዴ ላ ሙዚካ ካታላና’ በራሱ በዩኔስኮ የዓለም ቅርስነት የተመዘገበ አስደናቂ ሕንፃ ሲሆን፣ እንዲህ ባለው ታሪካዊ ቦታ ላይ የኢትዮጵያ ዜማ መሰማቱ የጥበብ ድንበር ተሻጋሪነትን ያሳያል።
ይህ ዝግጅት የኢትዮጵያን ሥነ-ጽሑፍ ከዓለም አቀፍ አዝማሚያዎች ጋር የሚያስተሳስር ከመሆኑም በላይ፣ በዕውቀቱ በሳቅና በቁም ነገር የታጀቡ ግጥሞቹን ለዓለም በማካፈል የአገራችንን ገጽታ በበጎ ጎኑ የሚያስተዋውቅበት ታላቅ አጋጣሚ ነው።
