ፕሬዝዳንት መንግሥቱ ኃ/ማርያም በሥልጣን ዘመናቸው የመሠረተ ትምህርት ዘመቻን ተግባራዊ ለማድረግ ላበረከቱት አስተዋፅዖ Ethiopian society partnership የተባለ ድርጅት ዕውቅና ሰጥቷቸዋል። ሽልማቱን ሐራሬ ዚምባብዌ በሚገኘው መኖሪያ ቤታቸው ተገኝቼ አስረክቤያቸዋለሁ።
በዚሁ ጊዜ ባደረጉት ንግግር ”መሃይምነትን ከሃገራችን ለማጥፋት የተደረገው ጥረት እሳቸው ወደ ሥልጣን ከመምጣታቸው በፊት በንጉሡ ዘመን ”የፊደል ሠራዊት”በሚል ለጎልማሶች ትምህር ይሰጥ እንደነበረ አስታውሰው የመሠረተ ትምህርት ዘመቻ በተጀመረ ጊዜ በመላው አገሪቱ በርካታ ሰዎች ተሠማርተው በሠሩት ሥራ አመርቂ ውጤት የተገኘበት መሆኑን ገልፀዋል።
””ሽልማቱ የኔ ብቻ ሳይሆን በወቅቱ የነበሩ አብዮታውያን ጓዶች፣ተማሪዎች፣ አስተማሪዎች፣ በጎ ፈቃደኞችና መላው ኅብረተሰብ በንቃት የተሳተፈበት ስለሆነ የነሱም ነውና ክብርና ምስጋናውን እነሱም ይውሰዱ” ብለዋል። አያይዘውም ”በዚያን ጊዜ ይህ መሃይምነትን ለማጥፋት የሠራውን መልካም ሥራ አስታውሰው ዕውቅና ለሰጡት ሁሉ ከፍ ያለ ምስጋናዬን አቀርባለሁ ”ብለዋል።
በዚሁ ሥነ ሥርዓት ላይ የተገኘችው ልጃቸው ዶክተር ትዕግሥት መንግሥቱ ”ለትምህርት ያለህ ጥማትና ፍላጎት ያኔ ገና በወጣትነትህ የተገለጠው የመጀመሪያ ልጅህን ”ትምህርት”ብለህ ስትሰይማት ነው። ”መማር መማር አሁንም መማር” የሚለው መፈክር የሁላችንም ትዝታ ነው። ትምህርት ለሁሉም እንዲዳረስ ያደግኸውን ጥረት በዚያ ተጠቃሚ የነበሩት ብቻ ሳይሆኑ ከመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ጋር እኛም ቤተሰቦችህ እናደንቃለን ”ብላለች።
ከጋዜጠኛ ገነት አየለ
