ኢትዮጵያ ካናዳን ጨምሮ ከአውሮፓ ሀገራት ጋር የስራ ስምምነት የላትም – የስራ እና ክህሎት ሚኒስቴር
ሳቢና ጄነራል ትሬዲንግ በተለያዩ የማህበራዊ ድረገጾች ላይ ተቀባይነትን ባገኙ ግለሰቦች ወደ ካናዳ እና አውስትራሊያ እልካለሁኝ በማለት ሲያስተዋውቅ መቆየቱ ተነግሯል።ድርጅቱ 22 በሚገኘው ቢሮው ላይ ሶስት ዓመታት ይህንን ስራ ሲሰራ ቆይቷል ።
በዚህም ታዋቂ በሚባሉ እና በማህበራዊ ድረገጾች ላይ ተጽዕኖ ፈጣሪ በሆኑ ግለሰቦች ማስታወቂያ በማስነገር በርካታ ገንዘብ በመቀበል ከዛሬ ነገ እያለ ለዓመት ያህል ሲያራዝም ቆይቶ አሁን ላይ ቢሮውን ዘግቶ ተሰውሯል ሲሉ ቅሬታ አቅራቢዎች ተናግረዋል።
ቅሬታቸውን ለብስራት ሬዲዮ ካቀረቡት መካከል ካናዳ ለመሄድ ከአንድ ሚሊዮን ብር በላይ ከከፈለች በኋላ የካናዳ ፕሮሰስ አልተሳካም ሌላ ሀገር ልሞከርልሽ ካልሆነ ተይው የሚል ምላሽ እንደተሰጣት እና አሁን ላይ ግለሰቡ ቢሮውን ዘግቶ መጥፋቱን ቅሬታ አቅራቢያችን ገልጸውልናል።
ሌላኛዋ ቅሬታ አቅራቢያቸን አውስትራሊያ ለመሄድ300 ሺህ ብር ክፍያ የከፈለች ሲሆን ካልተሳካ ሙሉ ክፍያውን እንደሚመልሱላት ቃል በመግባት ደረቅ ቼክ ሰጥተዋት እንደነበር ገልጻለች።
ይሁን እና ክፍያውን ከከፈለች ከቀናት በኋላ ድርጅቱ መዘጋቱን እንዲሁም ግለሰቡ ለምን ተዘጋ የሚል ጥያቄ በዋትስአፕ ሲያቀርቡለት በህመም ምክንያት ነው እንከፍታለን የሚል ምላሽ ቢሰጣቸውም ሶስት ወራት እንዳለፈው አንስታለች።
የሳቢና ጄነራል ትሬዲንግ ስራ አስኪያጅ የሆነው አቶ አለማየሁ ገብረጻድቅ በአሁን ሰዓት ከሀገር ውጪ በመሆናቸዉ ለማናገር ያደረገዉ ጥረት አልተሳካም፡፡ በተጨማሪም የተባለዉ መስሪያ ቤቱ መዘጋቱን አረጋግጠናል ፡፡
የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ለየትኛውም የጉዞ ወኪል ወይም ኤጀንሲ የሁለትዮሽ ስምምነት ወዳልተገባባቸው ሀገራት ዜጎችን ለሥራ እንዲያሰማራ የሰጠው ውክልናም ሆነ ፍቃድ የሌለ ሲሆን ኢትዮጵያ ካናዳን ጨምሮ ከየትኛውም የአውሮፓ ሀገር ጋር የሁለትዮሽ የሥራ ስምሪት ስምምነት እንደሌላትም ተገልጿል ።
ለብስራት ሬዲዮ
