በረመዳን ወር የምንተገብራቸው የመተሳሰብ፣ የመረዳዳትና መሰል መልካም እሴቶችን ሁልጊዜም የሕይወታችን ልምዶች ማድረግ እንደሚገባ የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ኡስታዝ አቡበከር አሕመድ ገለጹ፡፡
ኡስታዝ አቡበከር አሕመድ ለአዲስ ዘመን ጋዜጣ እንደገለጹት፤ ረመዳን መሠረታዊ እሴት በሰዎች ልብ ውስጥ የፈጣሪ ፍራቻ፣ መተዛዘን፣ ስለሌሎች መኖርን፣ መደጋገፍንና ማሰብን የሕይወታችን አካል እንድናደርግ ለ11 ወራት የሚሆን ስንቅ የሚይዝበት ወር ነው።
በመሆኑም በረመዳን ወር የምንተገብራቸውን የመተሳሰብ፣ የመረዳዳትና ለሌሎች መልካም እሴቶች ሁልጊዜም የሕይወታችን ልምዶች አካል ማድረግ ይጠበቅብናል ብለዋል።
ረመዳን አንዱ ስለሌላው የሚኖርበት ስለሆነ መልካም ተግባራት በስፋት የሚከናወኑበት ወር መሆኑን ጠቅሰው፤ ይህ ተግባር ደግሞ ሰዎች ዘወትር ሊኖራቸው የሚገባ ባሕሪ መሆን እንዳለበት ገልጸዋል።
እኛ ዋጋ ለማግኘት ብለን በፈቃዳችን ስንፆም ለችግር የተጋለጡ ወገኖቻችንን ማሰብና አለኝታነታችንን ማሳየት ይገባናል ብለዋል።
(ኢ ፕ ድ)
