“ቅድሚያ ለሰብዓዊ መብቶች” የተሰኘው ተቋም በትግራይ ክልል ውስጥ “አስገድዶ መሠወር” እና “ከሕግ ውጭ የኾነ እስር” በስፋት መንሰራፋቱን በማሳወቅ ከፍተኛ ስጋቱን ገልጿል።
የመንግሥት አካላት ለሚፈጸሙት ጥሰቶች ኃላፊነት የማይወስዱበትና ተጠያቂነት የሌለበት ሁኔታ መስፈኑን የጠቀሰው ተቋሙ፣ ይህም በክልሉ ያለውን የፍትህ ሥርዓት አሳሳቢ ደረጃ ላይ ጥሎታል ብሏል።
በተለይም ጋዜጠኞችና የፖለቲካ አስተያየት ሰጪዎች የሐሳብ ነፃነታቸውን በመጠቀማቸው ብቻ የዛቻና የማስፈራሪያ ዒላማ እየሆኑ መምጣቸው ተመላክቷል። ባለሥልጣናት በነፃነት ሐሳባቸውን በሚገልጹ ዜጎች ላይ የሚያደርሱትን ወከባ በአስቸኳይ እንዲያቆሙ ተቋሙ ጥብቅ ማሳሰቢያ ሰጥቷል።
ተቋሙ በመጨረሻም የክልሉ ጊዜያዊ አስተዳደር ያሉበት ባልታወቁ ሰዎች ዙሪያ ሙሉ መረጃ እንዲሰጥ ጥሪ አቅርቧል። በተጨማሪም በተሰወሩ ግለሰቦች ላይ “ገለልተኛ”፣ “ግልጽ” እና “አፋጣኝ” ምርመራ ተካሂዶ ውጤቱ ለሕዝብ ይፋ እንዲሆን በጽኑ ጠይቋል።
