በኢትዮጵያ የወጪ ንግድ ዘርፍ ታሪካዊ ምዕራፍ ተብሎ በተገለጸ ክስተት፣ ሞሃን ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር በአዲሱ የድሬዳዋ ነፃ የንግድ ቀጠና በኩል የአገሪቱን የመጀመሪያ የሦስተኛ ወገን የንግድ ልውውጥ በስኬት አጠናቀቀ።
ቀደም ሲል በኢትዮጵያ የሕግ ማዕቀፍ ተከልክሎ የነበረው ይህ የንግድ አሠራር፣ አንድ ድርጅት ምርትን ከአንድ አገር አቅራቢ ገዝቶ ወደ ሌላ አገር ገዢ በቀጥታ እንዲላክ የሚያደርግበትና ምርቱ ወደ ላኪው አገር ግዛት የማይገባበት የንግድ ሞዴል ነው።
የሞሃን ኩባንያ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ሀርሽ ኮታሪ ለካፒታል እንደገለፁት ፤ ይህ ስኬት ኢትዮጵያ በንግድ አገልግሎት ላይ የተመሠረተ የወጪ ንግድ ተግባር ውስጥ እንድትገባና የውጭ ምንዛሬ ገቢዋን እንድታሰፋ የሚያስችል መሆኑን ገልጸዋል።
እ.ኤ.አ. በኦገስት 2022 በይፋ ሥራ የጀመረው የድሬዳዋ ነፃ የንግድ ቀጠና የባንክ፣ የጉምሩክ፣ የፈቃድ አሰጣጥ እና የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን አገልግሎቶችን በአንድ ማዕከል አቀናጅቶ የያዘ ነው።
