ነባሩ የቱሪዝም ፖሊሲ 16 ዓመታት ያስቆጠረ ሲሆን ሲከለስ ፣አዲስ የሚፀድቀው ረቂቅ ፖሊሲ 7 መሰረታዊ የዘርፉን ችግሮች የሚፈታ እንደሆነ የቱሪዝም ሚኒስቴር ለአራዳ ኤፍ ኤም ገልጿል።
የሚኒስቴሩ የስትራቴጂክ አማካሪ ቴዎድሮስ ደርበው፥ በቅርቡ እንደሚፀድቅ የሚጠበቀው አዲስ ፖሊሲ በዘርፉ ያሉ ችግሮችን ከመፍታት አልፎ የሚኒስቴር መስሪያ ቤቱን ተቋማዊ አቅም የሚያጠናክር ነው ሲሉ ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ ቱሪስት አስጎብጂዎች ማህበር ፕሬዝዳንት ኤንዲ አሰፋ በበኩላቸው በፖሊሲ የሚፈቱ የአሰራር ክፍተቶች በመኖራቸው ባለፉት ጊዜያት እንደ ጥያቄ ይዘናቸው ከተነሳናቸው ጉዳዮች አንዱ የቱሪዝም ባለሙያዎች ወደ ዘርፉ ኢንቨስትመንት እንዲገቡ የሚያስችል የፖሊሲ ማዕቀፍ እንዲኖር ነው ብለዋል።
አንድ አስጎብኚ ድርጅት ለመክፈት ከ5 ዓመት በላይ ያላገለገለ አንድ ‘ሚኒ ባስ’ ወይንም ‘ስቴሽን ዋገን’ መኪና ያስፈልግ እንደነበረና ባለሙያው ይህን የማድረግ አቅም የሌለው በመሆኑ በዘርፉ በበቂ ሁኔታ መስራት ሳይችል እንደቆየ ለጣቢያችን አስረድተዋል።
አሁን ግን አስጎብኚዎች በልምድ እና በሙያቸው ታግዘው በኪራይ ተሽከርካሪዎች መስራት የሚችሉበት እና ዘርፉ በእነሱ የሚያዝበት ዕድል በቀጣይ እንደሚኖር ተስፋ እናደርጋለን ሲሉም አክለዋል።
