በኦሮሚያ ክልል የውጪ ዜጎች በኢትዮጵያ ውስጥ ብቻ የሚገኘውን የደጋ አጋዘን በ15 ሺህ ዶላር እያደኑ መሆኑን የክልሉ አካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን አስታወቀ።
የኦሮሚያ ክልል አካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ ቦና ያዴሳ፤ “የውጪ ዜጎች አንድ አጋዘን ለማደን 15 ሺህ የአሜሪካ ዶላር ይከፍላሉ፤ ያደኑትንም አጋዘን ከአንገት በላይ ያለው አካል ይዘው መሄድ ይችላሉ” ብለዋል።
ዋና ዳይሬክተሩ፤ የደጋ አጋዘን በአርሲና ባሌ ተራራማ ስፍራዎች እንዲሁም በምዕራብ ሀረርጌ በስፋት የሚገኝ መሆኑን ጠቅሰው፣ የውጪ ሀገር ዜጎችም ለስፖርታዊ አደን የሚመርጡት ብርቅዬ እንስሳ መሆኑን ተናግረዋል።
አሁን ላይ በአዳባና ዶዶላ አካባቢዎች ኢንተርፕራይዞች ተደራጅተው፣ ለውጪ ዜጎች የደጋ አጋዘንን ለአደንነት እንዲያቀርቡ መደረጉን ገልጸዋል፡፡
አደኑን የሚያደርጉት የውጪ ዜጎች ፈቃድ የሚሰጣቸው ሲሆን፤ በአካባቢው ከተደራጁ ኢንተርፕራይዞች ጋር በመሆን ያረጀ ወንድ የደጋ አጋዘን ተመርጦ እንዲያድኑ ይደረጋል ሲሉ ለኢፕድ ተናግረዋል።
ማንኛውንም የደጋ አጋዘን ማደን ፈጽሞ የተከለከለ መሆኑንም አክለዋል፡፡ ከአደኑ የሚገኘው ገቢ 70 በመቶ ለኢንተርፕራዞች የሚገባ መሆኑና 30 በመቶውን መንግስት እንደሚወስድም አቶ ቦና ተናግረዋል፡፡
