በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላንና ፣ በጀት እና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰኔ 15 ቀን 2018 ዓ.ም የአስረጂ ወይይት ያካሄደበት የካርበን ገበያ ረቂቅ አዋጅ ባንኮች በካርበን ግብይት አንዲሳተፉ ይፈቅዳል።
ረቂቅ አዋጁ የተበታተነውን የካርበን ግብይት በአንድ የሕግ ማዕቀፍ ለማስተዳደር እና የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል እየተከናወኑ ያሉ ጅምር ስራዎችን ለማጠናከር እንደሚረዳ ተነግሯል።
ኢትዮጵያ ለአየር ንብርት ለውጥ ተጋላጭ መሆኗን ያስታወሰው የካርበን ረቂቅ አዋጅ ለአማቂ ጋዝ ልቀት ቅነሳ ደጋፍ ማድረግ እና በአየር ንብርት ለውጥ ላይ አደገኛ ጣልቃ ገብነትን ማስቀረት “የብሔራዊ ጥቅም ጉዳይ ነው” ብሏል።
በአስር ክፍል በ44 ገጽ የተሰናደው የካርበን ረቂቅ አዋጅ የኢትዮጵያ በጉዳዩ ላይ በአለም አቀፍ ደረጃ የተፈራረመችውን ስምምነት ለመተግበርም እንደሚረዳ በአላማዎቹ ስር ተጠቅሷል።
ረቂቁ ስለ ፋይናንስ ድንጋጌዎች በሚዘረዝርበት ክፍል ዘጠኝ ላይ የባንኮችና ሌሎች የፋይናንስ ተቋማት ተሳትፎ እና ሚና ሲያስረዳ ፤ ባንኮች እንደየፍላጎታቸው በገዥነት፣ በሻጭነት፣ በግብይት አከናዋኝነት ወይም አሰባሳቢነት ሊሳተፉ ይችላሉ ይላል።
የካርበን አሰባሳቢ የሚለው ሲተረጉመው ደግሞ ፤ ከተለያዩ የመሬት ባለይዞታዎች ፣ ኩባንያዎች አነስተኛ የሙቀት አማቂ ጋዞችን የመቀነስ፣ የማስወገድ ወይም የማስቀረት ፕሮጀክቶችን በአንድ ላይ በማሰባሰብ ወደ ልዩ ልዩ ፖርቶፎሊዮች በማካተት እንደገና የሚሸጥበትን መንገድ የሚመራ ነው ሲል ተርጉሞታል።
በተጨማሪም ባንኮች የካርቦን ሃብት ፖርቶፊሊዮችን ከአካባቢ እና ከማህበራዊ ስጋት አስተዳደር ማዕቀፎቻቸው ጋር እንዲገናኙ ይበረታታሉ ፣ ከካርበን ክሬዲት ጋር የሚያያዙ ቦንዶችን እና “አረንጓዴ ዋስትናዎችን “ጨምሮ ልዪ የፋይናንስ አግልግሎቶችን ማቀረብ እንደሚችሉ አስረድቷል።
ኢትዮጵያ ውስጥ ያሉ ባንኮች ፣ የፋይናንስ ተቋማት በሀገሪቱ ለሚከናወኑ የሙቀት አማቂ ጋዞችን ልቀት ለመቀነስ ፣ ለማስቀረት አልያም ለማስወገድ ለተቀረጹ ፖሊሲዎች የብድር ፋይናንስ ፣ የኢኪዮቲ ኢንቨስትመንት እና የብድር ገጽታ፣ ማሻሻያዎችን ሊያቀርቡ እንደሚችሉም በረቂቁ ተደንግጓል።
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ የፋይናንስ ተቋማት ለካርበን ክሬዲቶች ግብይት ፣ ዝውውር እና ክፍያ እንደ አሳላጫ ወይም ባለዳራዎች መሆን እንደሚችሉም ተጠቅሷል።
በካርበን ገበያ ረቂቅ አዋጅ ላይ ወደፊት የሕዝብ ይፋዊ ውይይት መድረክ እንደሚካሄድ ተነግሯል።
