በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል በማዕድን ዘርፍ እየተተገበረ ባለው የሕግ ማሕቀፍ እና የክትትል ሥራ ባለፉት ሰባት ወራት ከ50 ኩንታል በላይ ወርቅ ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ገቢ መደረጉን የክልሉ ማዕድን ሀብት ልማት ቢሮ አስታወቀ።
ምክትል ቢሮ ኃላፊው አቶ ናስር መሀመድ እንደገለፁት፤ በ2017 በጀት ዓመት በአጠቃላይ 47 ኩንታል ወርቅ ለብሔራዊ ባንክ ገቢ ተደርጎ የነበረ ሲሆን፣ በተያዘው የ2018 በጀት ዓመት ሰባት ወራት ብቻ የቀረበው የወርቅ መጠን የዓምናውን ጠቅላላ ዓመት የሚበልጥ መሆኑን ጠቁመዋል።
ክልሉ እስከ በጀት ዓመቱ መጨረሻ 70 ኩንታል ወርቅ ለመሰብሰብ አቅዶ በቁርጠኝነት እየሠራ ይገኛል ብለዋል።
ይህ ስኬት ሊመዘገብ የቻለው ቀደም ሲል የነበሩ ሕገወጥ ድርጊቶችን ለመከላከል አምራቾች እና አቅራቢዎች ሕጋዊ ፈቃድ ወስደው እንዲሠሩ በመደረጉና አቅራቢዎች ወርቅ ገዝተው በሕጋዊ መንገድ ወደ ባንክ የሚያስገቡበት የአሠራር ሥርዓት በመዘርጋቱ ነው።
በተጨማሪም የክልሉ መንግሥት እና የጸጥታ አካላት በቅንጅት በመሥራት “የክልሉን ሰላም ማስጠበቃቸው” ወርቅ ሕጋዊ በሆነ መንገድ ለባንክ እንዲገባ ትልቅ አስተዋጽኦ አድርጓል። (ኢፕድ)
