የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከኢራን ጋር ያለውን ጦርነት ለማቆም ከሚደረገው ድርድር ጎን ለጎን፥ የአረብ እና የሙስሊም አገራት መሪዎች ከእስራኤል ጋር ያላቸውን ግንኙነት ወደ መደበኛነት እንዲቀይሩ እና «የአብርሃም ስምምነትን» እንዲቀላቀሉ ይፋዊ ጥያቄ ማቅረባቸው ተሰማ።
ባለፈው ቅዳሜ የተካሄደውን የስልክ ውይይት አስመልክቶ የወጡ መረጃዎች እንደሚያመለክቱት፥ ፕሬዝዳንት ትራምፕ ከኢራን ጋር የተኩስ አቁም ስምምነት ላይ ከተደረሰ በኋላ ቀጣዩ ትልቅ ቀጣናዊ እርምጃ ከእስራኤል ጋር ሰላም የመፍጠር ሂደት እንዲሆን ይፈልጋሉ ተብሏል።
ትራምፕ ባደረጉት የጋራ የስልክ ውይይት የሳውዲ አረቢያ፣ የተባበሩት አረብ ኤምሬትስ፣ የኳታር፣ የቱርክ፣ የፓኪስታን፣ የግብፅ፣ የዮርዳኖስ እና የባህሬን መሪዎች ተሳትፈዋል።
ፕሬዝዳንቱ በማህበራዊ ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት፥ ከኢራን ጋር የሚደረገው ስምምነት የመካከለኛው ምስራቅ አገራት ታሪካዊውን የአብርሃም ስምምነት በመቀላቀል ረገድ በሚያሳዩት ትብብር ይበልጥ እንደሚጠናከር ገልጸዋል።
እንደ ሳውዲ አረቢያ እና ኳታር ያሉ አገራት ከእስራኤል ጋር ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ለመጀመር የፍልስጤም መንግስት መመስረትን እንደ ቅድመ ሁኔታ ማስቀመጣቸው ይታወቃል። ጀሩሳሌም ፖስት እና አልጀዚራ እንደዘገቡት ፡፡
