የኦሮሞ ነጻነት ግንባር (ኦነግ) ሊቀመንበር አቶ ዳውድ ኢብሳ በኦሮሚያ ክልል በተለይም ሊወዳደሩበት በታቀደው የሆሮ ጉድሩ አካባቢ ባለው አስከፊ የፀጥታ ሁኔታ ምክንያት በዘንድሮው 7ኛው አገራዊ ምርጫ እንደማይሳተፉ ድርጅቱ ማስታወቁ ተዘግቧል።
የፓርቲው የዲሲፒሊን እና ቁጥጥር ኮሚቴ ሊቀመንበር አቶ አለማየሁ ዲሮ እንደገለጹት፣ ሊቀመንበሩ ባይወዳደሩም በእሳቸው የምርጫ ክልል ሌላ ዕጩ ተተክቷል።
ኦነግ በ6ኛው አገራዊ ምርጫ “ከፖለቲካው ተገፍቻለሁ” በሚል ሳይሳተፍ መቆየቱ የሚታወስ ሲሆን፣ ዘንድሮ ወደ ውድድሩ የተመለሰው የፖለቲካ ምኅዳሩ ተሻሽሎ ሳይሆን ከምርጫ ቦርድ ጋር ለመገናኘት መጠነኛ ዕድል በማግኘቱ መሆኑ ተመልክቷል።
ፓርቲው በአሁኑ ወቅት ካሉት 230 ቢሮዎች ውስጥ ክፍት ሆኖለት የሚገኘው የአዲስ አበባው ቢሮ ብቻ በመሆኑ፣ ለዘንድሮው ምርጫ ማቅረብ የቻለው 128 ዕጩዎችን ብቻ እንደሆነ ተገልጿል።
ከእነዚህም ውስጥ ግማሽ ያህሉ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት፣ 50 ለኦሮሚያ ክልል ምክር ቤት፣ ቀሪዎቹ ደግሞ በአማራ፣ ቤንሻንጉል ጉሙዝ፣ አዲስ አበባ፣ ድሬዳዋ እና ሐረሪ ክልሎች የሚወዳደሩ ናቸው።
አቶ አለማየሁ አክለውም፣ ድርጅቱ በአሁኑ ወቅት ምክትል ፕሬዝዳንት የሌለው ሲሆን፣ ሌሎች ከፍተኛ አመራሮችም በተለያዩ “የግል ምክንያቶች” ለዕጩነት እንዳልቀረቡ አስረድተዋል።
ኢትዮጵያ ኢንሳይደር
